
ለዝች ደብዳቤ ከአሌክሶ ሰዕል ወጪ የሚሆን ማገኘት አልቻልኩም፤ አሌስ ሰዕልህ ይባረክ!
የአንዲት እናት ደብዳቤ፤
ይድረስ በውጪ ሃገር ለምትኖሪው ውድ ልጄ፤
ባለፈው ሰሞንልሽ… ያቺ ከበታቻችን ያለችው ቀጭኗ ሴትዮ… ምነው እንኳ ቀበሌ ገባ ወጣ የምትለው… እ… እርሷ ወደቤታችን ብቅ ብላ ነበር። እና ታድያ፤ ዲያስፖራዋ ልጅዎ እንዴት ነች… ብላ ብትጠይቀኝ ጊዜ ኧረ እኔ እንዲህ የምትባል ልጅ የለችኝም ፍቅርዬ አበራ… ማለትሽ ነው… ብዬ ጠይኳት፤ እርሷቴ ”በውጪ ሀገር የሚገኝ ማንኛውም ሰው ዲያስፖራ ነው የሚባለው” ብላ ነገረችኝ። አከል አድርጋም፤ ”በልማቱ ተሳታፊ ከሆነች ልማታዊ ዲያስፖራ ልማቱን አደናቃፊ ከሆነች ደግሞ የቀድሞ ስርአት ናፋቂ ነው የምትባለው!” ስትል ጨመረችልኝ፤ እኔም እንዳላወቀ እንዳልገባው ሆኜ፤ የወደፊቱ ስርዓት ናፋቂዎች የሚባሉስ የሉም…. ብዬ ብላት፤ ”ምን አሉኝ….” ብላ ስተደናበር፤ የለ…. እንደው ለቤተሰብ ሳታሳውቁ ስም መለዋወጥ ምን ይሉት ፈሊጥ ነው… ብዬ ገርሞኝ ነው…. እያልኩ፤ ሳዳርቃት ዋልኩልሽ… እንዲህ በሆነ ባለሆነ ያዝ ካላደረግናቸው የነርሱ ፓለቲካ ማለቂያም የለው ልጄ….
የሆነው ሁኖ… አንቺ እንዴት አለሽልኝ፤ እኔ እናትሽ ካንቺ ሃስብ እና ናፍቆት በቀረ እጅጉን ደህና ነኝ።
እንዳልኩሽ፤ ሰሞኑን የቀበሌ ሰዎች ወደቤት መጣ መጣ ማለት አብዝተውብናል… ምክኝያቱ ምን እንደሁ እስቲ ከእኛ እናንተ ታውቁታላችሁና ምን ፈልገው እንደሆነ አጣርተሽ ነግሪኝ፤ እውነቴን ነው ልጄ እንደውም አሁን ይቺን ኢሳቴን ከተከልኩ ኋላ ትንሽ ሻል አለኝ እንጂ ድሮማ ኢቶጵያ ቴሌቪዥን የሚለንን ብቻ እየሰማን የመረጃ ድርቅ ገብቶን ነበር። እርግጥ አንዳንድ ወቅት ዜናውን ገልብጦ በመስማት እውነቱን እንረዳዋለን ለምሳሌ፤ ”አንዳንድ አሸባሪዎች በቁጥጥር ስር ዋሉ” የሚል ዜና የተነገረ እንደሆነ አንድንድ ጀግኖች እና ለሀገር ያገባኛል የሚሉ ወገኖች፤ ታግተዋል ማለት ነው… ብለን እየተረጎምን ሃቋን እናገኛታለነ!