(በላይ ማናዬ)
‹‹እኔ ጆርጅ ቡሽን (ፕሬዚዳንት) አላደንቅም፤ ጠፈር ላይ የወጡትንም አላደንቅም፡፡ የማደንቀው እነዚህን ሰዎች ለትልቅ ደረጃ ያደረሷቸው መምህራንን ነው፡፡››
መምህራን የሀገር ምሰሶዎች… መምህርነት የሙያዎች አባት… መምህር የእውቀት ብርሃን…ይህ እውነት ነው፡፡ እውነቱ ግን ዛሬ ላይ ተጋርዷል፡፡ መምህርነትም ሆነ መምህራን የነበራቸው ክብር ዛሬ ላይ በኢትዮጵያ መሬት በአስደንጋጭ ፍጥነት እየወረደ ይገኛል፡፡ መምህራን በሙያቸው እያፈሩ ነው፡፡ እውቀታቸውን እየሰሰቱ ነው፡፡ አዎ፣ መምህራን ጫንቃቸው ጎብጦ ነገን በደበዘዘ ተስፋ የሚጠባበቁ ‹ምስኪኖች› እየሆኑ ነው፡፡ ግን እንዴት?
ካድሬነት Vs መምህርነት
ወጣት ነው፤ ገና ለስራው ዓለም ብዙ አበርክቶት የሚጠበቅበት፡፡ ወጣቱ በአዲስ አበባ አብዮት ቅርስ መሰናዶ ት/ቤ የኬሚስትሪ መምህር ነው፡፡ በስራው ዓለም ለአራት ዓመታት ያህል ቆይቷል፡፡ በእነዚህ ዓመታት ግን የሚሽተው ሙያዊ ተግባሩን ለመወጣት ከብዶታል፡ ፡ መምህርነቱን የሚፈታተኑ በርካታ ጉዳዮች እየተፈራረቁበት ተቸግሯል፡ ፡ ወጣቱ ትዳር መሥርቶ፣ ወልዶና ከብዶ መኖር ቀርቶ ጥሩ ጫማና ልብስ ገዝቶና ጥሩ ምግብ ተመግቦ ለመኖር እንኳ እንዳቃተው ይናገራል፡ ፡ ከተማሪዎቹ በታች እየሆነ የሚታይበትን የኑሮ ጫና መቋቋም እንደተሳነውም ይገልጻል፡፡ በዚህ ሁኔታም ሆኖ ማስተማር ይፈልግ ነበር፡፡ ዳሩ ግን መምህርነቱ ከዚህም በላይ ፈተና አሳይቶታል፡፡ ነጻነቱን ነፍጎታል፡፡
የፖለቲካ ሰዎች (ካድሬዎች) የሚያስተምርበት ድረስ እየሄዱ ተጽዕኖ ያደርጉበታል፡፡ ት/ቤቶች የእውቀት ማበልፀጊያና መጋሪያ ደጆች ቢሆኑም አሁን አሁን ስልጣን ፈላጊዎች መናሃሪያ አድርገዋቸዋል፤ የፖለቲካ ማዕከላት ሆነዋል፡፡