Monday, April 14, 2014

የመምህራን ፍዳ


(በላይ ማናዬ)

teacher1
‹‹እኔ ጆርጅ ቡሽን (ፕሬዚዳንት) አላደንቅም፤ ጠፈር ላይ የወጡትንም አላደንቅም፡፡ የማደንቀው እነዚህን ሰዎች ለትልቅ ደረጃ ያደረሷቸው መምህራንን ነው፡፡››
መምህራን የሀገር ምሰሶዎች… መምህርነት የሙያዎች አባት… መምህር የእውቀት ብርሃን…ይህ እውነት ነው፡፡ እውነቱ ግን ዛሬ ላይ ተጋርዷል፡፡ መምህርነትም ሆነ መምህራን የነበራቸው ክብር ዛሬ ላይ በኢትዮጵያ መሬት በአስደንጋጭ ፍጥነት እየወረደ ይገኛል፡፡ መምህራን በሙያቸው እያፈሩ ነው፡፡ እውቀታቸውን እየሰሰቱ ነው፡፡ አዎ፣ መምህራን ጫንቃቸው ጎብጦ ነገን በደበዘዘ ተስፋ የሚጠባበቁ ‹ምስኪኖች› እየሆኑ ነው፡፡ ግን እንዴት?
ካድሬነት Vs መምህርነት
ወጣት ነው፤ ገና ለስራው ዓለም ብዙ አበርክቶት የሚጠበቅበት፡፡ ወጣቱ በአዲስ አበባ አብዮት ቅርስ መሰናዶ ት/ቤ የኬሚስትሪ መምህር ነው፡፡ በስራው ዓለም ለአራት ዓመታት ያህል ቆይቷል፡፡ በእነዚህ ዓመታት ግን የሚሽተው ሙያዊ ተግባሩን ለመወጣት ከብዶታል፡ ፡ መምህርነቱን የሚፈታተኑ በርካታ ጉዳዮች እየተፈራረቁበት ተቸግሯል፡ ፡ ወጣቱ ትዳር መሥርቶ፣ ወልዶና ከብዶ መኖር ቀርቶ ጥሩ ጫማና ልብስ ገዝቶና ጥሩ ምግብ ተመግቦ ለመኖር እንኳ እንዳቃተው ይናገራል፡ ፡ ከተማሪዎቹ በታች እየሆነ የሚታይበትን የኑሮ ጫና መቋቋም እንደተሳነውም ይገልጻል፡፡ በዚህ ሁኔታም ሆኖ ማስተማር ይፈልግ ነበር፡፡ ዳሩ ግን መምህርነቱ ከዚህም በላይ ፈተና አሳይቶታል፡፡ ነጻነቱን ነፍጎታል፡፡
የፖለቲካ ሰዎች (ካድሬዎች) የሚያስተምርበት ድረስ እየሄዱ ተጽዕኖ ያደርጉበታል፡፡ ት/ቤቶች የእውቀት ማበልፀጊያና መጋሪያ ደጆች ቢሆኑም አሁን አሁን ስልጣን ፈላጊዎች መናሃሪያ አድርገዋቸዋል፤ የፖለቲካ ማዕከላት ሆነዋል፡፡

የሽብርተኝነት እንቆቅልሽ


የኢትዮጵያው አዋጅ ትርጓሜና ክፍተቶቹ

terror
መንግስታት በተለያየ መልኩ ትርጉመው ያቀረቡትን ሽብርተኝነት ለመዋጋት በሚል ህግ ያወጣሉ፡፡ በእርግጥ በአዲስ መልክ በሽብር ላይ የታወጀው ዘመቻ በአሜሪካ ግፊት የመጣ ነው፡፡ እ.ኤ.አ በ2001 አሜሪካ ከደረሰባት የሽብር ጥቃት በኋላ “war on terror” እንዲሁም “counter ter­rorism” የተሰኙ ዘመቻዎችን ነድፋ ተንቀሳቅሳለች፡፡ አሜሪካ ወዳጅም ሆነ የቀዩ ባላንጣዎቿን ሳይቀር ደልላም ሆነ ተማጽና የጀመረችው ይህ “ጸረ ሽብር ዘመቻ” መንግስታት በየ አገራቸው የራሳቸውን ጥቅም የሚያስጠብቁ አፋኝ “የጸረ ሽብር” ዘመቻ እንዲያወጡ እድል ሰጣቸው፡፡ አሜሪካ የሰብአዊ መብት ይጥሳሉ እያለች ስትወቅሳቸው የነበሩ ስርዓቶች ሳይቀሩ የተደላደለ የዴሞክራሲያዊ መሰረት ባልተጣለበት ሁኔታ ዴሞክራሲያዊና ሰብአዊ መብቶችን የሚደፈጥጡ አዋጆች አጽድቀው ሲተገብሩ ከሀያሏ አገር የገጠማቸው ወቀሳና ግፊት ከዚህ ግባ የሚባል አይደለም፡፡ በተቃራኒው አልቃይዳንና ቅርንጫፎቹ አሊያም ተያያዥ አሸባሪና አክራሪ የምትላቸውን ሁሉ እንዲያድኑ ወታደራዊ ድጋፍን አጋብሰዋል፡፡ ኢህአዴግ መራሹ የኢትዮጵያ መንግስት ከኒዮርኩ ጥቃት በኋላ አጋጣሚውን ከተጠቀሙት መንግስታት መካከል አንዱ ነው፡፡
አሜሪካ መራሹ ከሆነው በተጨማሪ በተለይም የምዕራባዊያን አገራት የደረሰባቸውን አደጋም አስከትለው ህጎችን አውጥተው ተግብረዋል፡፡ አብዛኛዎቹ ጸረ ሽብር ህጎች መንግስታት ራሳቸው ያጸደቋቸውን ህጎች ሳይቀር ጥሰው ሽብርተኝነት ያሉንት ወንጀል እንከላከላለን የሚልባቸው ህግጋቶች ናቸው፡፡ በተለይ ዴሞክራሲ ባልተጠናከረባቸው አገራት እነዚህ ህጎች አምባገነኖች በአገራቸው ህዝብ ላይ ያሹትን እንዲፈጽሙ እና ህጉን ተገን አድርገው ለረዥም ጊዜ ስልጣን ላይ እንዲቆዩ ምክንያት እየሆነላቸው ይገኛል፡፡
የአዋጁ አውድ
በአሁኑ ወቅት በዓለም ላይ የሚገኙት የተለያዩ የሽብር ትርጉሞች የሚተረጎሙት በዝርዝር ተግባራት (ግድያ፣ ጠለፍ፣ እገታ፣ በመሳሰሉት ድርጊቶችና) እና ከተፈጸሙት ድርጊቶች በስተጀርባ አሉ የሚባሉት (አብዛኛዎቹ መንግስታት ራሳቸው ከጥቅማቸው አንጻር የሚተረጉሟቸው ናቸው) በዓላማና ፍላጎትን በማጣመር ነው፡ ፡ የኢትዮጵያ የጸረ ሽብር አዋጅ ትርጓሜም ይህንኑ መንገድ የተከተለ ነው፡፡ አዋጅ 652/2001 በድርጊት በኩል ሽብርተኝነትን ሲተረጉም፡-
  1. ሰውን የገደለ ወይንም በአካሉ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያደረሰ እንደሆነ
  2. የህብረተሰቡን ወይንም የህብረተሰቡን ክፍል ደህንነት ወይንም ጤና ለከፍተኛ አደጋ ያጋለጠ እንደሆነ
  3. እገታ ወይንም ጠለፋ የፈጸመ እንደሆነ
  4. በንብረት ከፍተኛ ጉዳት ያደረሰ እንደሆነ
  5. በተፈጥሮ ሀብት፣ በአካባቢ፣ በታሪካዊ ወይንም የባህል ቅርስ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያደረሰ እንደሆነ
  6. ማንኛውንም የህዝብ አገልግሎት ለከፍተኛ አደጋ ያጋለጠ፣ የያዘ፣ በቁጥጥር ስር ያደረገ፣ ያቋረጠ ወይንም ያበላሸ እንደሆነ ወይንም
  7. ከላይ የተጠቀሱትን ለመፈጸም የዛተ እንደሆነ በሽብርተኝነት እንደሚወነጀል ይገልጻል፡፡ ለጥፋቱም ከ15 አመት ጀምሮ የእድሜ ልክ ብሎም የሞት ቅጣት እንደሚያስወስንበት አስቀምጧል፡፡
ከላይ ከተጠቀሱት መካከል አብዛኛዎቹ ዝርዝሮች ህጉ ተወሰደባቸው ከሚባሉት የዴሞክራሲያዊ አገራት ጸረ ሽብር ህግ ያልተካተቱ ናቸው፡፡ ለምሳሌ ያህል “ማንኛውንም የህዝብ አገልግሎት ለከፍተኛ አደጋ ያጋለጠ፣ የያዘ፣ በቁጥጥር ስር ያደረገ፣ ያቋረጠ ወይንም ያበላሸ” የሚለው በሰላማዊ እምብይተኝነት ጊዜ የሚፈጸምና በሌሎች አገራት ሽብርተኝነት ቀርቶ ተራ ወንጀል ስምም አያስከስስም፡፡

Thursday, April 10, 2014

ከአገር መውጣት የማይችሉ ባለሥልጣናት በጭንቀት ውስጥ ናቸው


"አሁን ያለው ኢህአዴግ ላዩ በቀለም ቀቢ የተዋበ ይመስላል"

stressed
ኢህአዴግ በሙስና ስም የ”ማጥራት ዘመቻ” ማካሄዱን ተከትሎ የተከሰተው አለመተማመንና እርስ በርስ በጥርጥር የመተያየት ችግር ካድሬውን ማስጨነቁ ተጠቆመ። ኢህአዴግን ለመሰናበት የሚፈልጉ በርካታ ካድሬዎች “ለምን” በሚል የሚቀርብላቸውን ጥያቄ በመፍራት የግድ ፓርቲውን መስለው እንደሚኖሩ ተገለጸ።
የጎልጉል የአዲስ አበባ ዘጋቢ ቀደም ሲል ኢህአዴግን ተሰናብተው የወጡና በተለያዩ የውጪ ድርጅቶች ውስጥ ተቀጥረው በማገልገል ላይ ካሉ ያገኘውን መረጃ በመጥቀስ እንደዘገበው፣ የቀድሞ የትግል ጓደኞቻቸው “በደህና ጊዜ ተገላገልክ” በሚል በፓርቲው ውስጥ ችግር ስለመኖሩ እየነገሯቸው ነው። አብዛኞቹ ኢህአዴግን ተለይተው በሰላም ስለመኖር እንደሚያስቡ ነው የተሰማው።
የቤተሰቦቻቸው የወደፊት እድልና የነሱ በፍርሃትና በጭንቀት መኖር አሳዛኝ እንደሆነ የነገሩት የቀድሞ የኢህአዴግ ሰዎች “አሁን ያለው ኢህአዴግ በቀለም ቀቢ የተዋበ ይመስላል” በማለት አንድ በሚኒስትር ዲኤታ ማዕረግ እያገለገለ ያለ የቀድሞ ጓደኛቸው እንደነገራቸው ገልጸዋል።
ለስራ እንኳን ካገር መውጣት የማይችሉ ባለስልጣኖች እንዳሉ ዘጋቢያችን አመልክቷል። በተቀመጡበት ሃላፊነት ወደ ውጪ የሚያስኬድ አጋጣሚ ሲኖር የሚከለከሉ እንዳሉም ያገኛቸውን መረጃዎች ጠቅሶ ዘግቧል። ለሃላፊዎቹ ደህንነት ሲባል የሚሰሩበትን ተቋምና ስም መናገር እንደማይችሉ በመጥቀስ መረጃውን የሰጡት ክፍሎች “ባለስልጣኖቹ በመካከላቸው እርስ በርስ መተማማን ስለማይችሉ ችግራቸውን መወያየት እንኳን አይችሉም” ብለዋል፡፡
“በጣም የሚቀርቡኝ ጓደኞቼ ገንዘብ ወደ ውጪ እንድወስድላቸው እስከመጠየቅ ደርሰዋል” ሲሉ የገለጹት የቀድሞ የኢህአዴግ ባለስልጣን፣ ፓርቲው በሙስና ስም ያካሄደው የሽግግር ወቅት የማጥራት ርምጃ የፈጠረው ስሜት አሁን ድረስ እንዳለ ጠቁመዋል።

Wednesday, April 9, 2014

ዲና ሙፍቲ ይመችዎት – “በነጻው ፕሬስ” ስም


ቀጭኑ ዘ-ቄራ

dina_mufti
ለምሳሌ አንድ አናጢና ግንበኛ የነበረ ሰው ጊዜ ረድቶት ወይም ተምሮ ወይም እድገት አግኝቶ ወይም …. በቃ በሆነ ነገር የጦር ጄኔራል ቢሆንና ተመልሶ ግንበኛ ቢሆን ምን ተብሎ ሊሰየም ነው? ግራ ያጋባል። ግን ደግሞ ላያጋባም ይችላል። የዛሬዎቹ ጄኔራሎች ኢንቨስተር ስለሆኑ ነዋ!! ለምሳሌ አንድ አምባሳደር ተብሎ የ”ተመደበ” ሰው፣ በግምገማ በሉት በገገማ “በቃህ” ቢባልና ቀድሞ ወደነበረው ሙያ ወደ ነርስነቱ ቢመለስ ምን ተብሎ ሊጠራ ነው? “አምባሳደር፣ ነርስ፣ እገሌ …”?
ቀጭኑ ዘ-ቄራ ነኝ። በውል በማይገባችሁ ምክንያት ተሰውሬ ነበር። ዛሬ እግር ጣለኝና “ላሸብር” መጣሁ። ሰላምታዬ መሆኑ ነው። መለስ ድንጋዩ ይቅለላቸው፣ አርማታው ስፖንጅ ይሁንላቸውና ብዙ አይነት የሰላምታ ቋንቋና ስታይል “አውርሰውን” አልፈዋል። ታላቁና አርቆ አስተዋዩ መሪያችን!! ህወሃቶች በዚህም ይቀኑ ይሆናል እኮ። መለስዬን ማን የነሱ ብቻ አደረጋቸው? እስኪ አርፈው ይተኙ፣ ይሙቱበት… እኔ ወደ ጉዳዬ ላምራ። “ግን መቃብራቸው ልዩ ጥበቃ የማይደረግለት ለምንድነው?” ሳልል ማለፍ አልፈልግም። ዋ!! ድንገት ቢነሱ!! ዋ ብያለሁ …
ግን አሁን አምባሳደር የነበረ ሰው ጡረታ ወጥቶ ደላላ ቢሆን “አምባሳደር፣ ደላላው፣ እገሌ” እያልን ልንጠራ ነው? የአገራችን ሚዲያዎች ነጻ መውጣት ያቃታቸው ከስም ስያሜ ጀምሮ ነው። ካላይ ያነሳኋቸው የኢህአዴግ ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ “አቶ” ይቅርታ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ስም ነው ሌላ ጉዳይ ውስጥ ቀርቅሮ ያስለፈለፈኝ። እሳቸው አሁን የተመደቡበት መደብ “አምባሳደር” በሚል ርዕስ ከሆነ ግድ የለኝም። ግን ለጌቶቻቸው ቀላጤ ሆነው በህዝብ ግንኙነትና አንደበትነት ተመድበው ከሆነ ለጊዜው “አቶ” በቂ ነው። የነጻው ፕሬስ ሰዎች ወይም የበርጫ ቤት ባልደረባዬ ሽመልስ ከማል እርማት ይስጡበት።

Monday, April 7, 2014

የኛና የነሱ ኢትዮጵያ


(ናትናኤል ካብትይመር)
rvp
እኛ የምናውቃት ኢትዮጵያ ከግማሽ በላይ ህዝቧ በመብራትና በውሃ እጦት የሚሰቃይባት ፣ በስልክና በኔትወርክ ችግር የሚማረርባት ፣  በመልካም አስተዳደር እጦት አሳሩን የሚበላባት ፣  አብዛኛው ህዝቧ የዛሬን እንጂ የነገን ማቀድ የማይችልባት፣ የተለያዩ ተንታኞችና አለማቀፍ ድርጅቶች “ችግር አለ” ብለው የሚያስጠነቅቋት ፣ ለዲሞክራሲ ፈር ቀዳጅ መሆን የሚገባው የፖለቲካ ስርዓት የሚያስፈራና ደም ደም የሚሸትባት ፣ ብዙ ዜናና ትንታኔ ስለ አንዲት የመንግስት ፕሮጀክት ለአመታት የሚነገርባት ፣ ከአንዲት ፕሮጀክት ብዙ ሚሊዮን ብር በሙስና ተዘርፎ ጥቂቶች የሚከብሩባት ፣ መንግስት ተብየው ሃገርና ህዝብ ከማስተዳደር ይልቅ ስልጣኑን ለማደላደል ተግቶ የሚሰራባት ፣ በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ዜጎቿን በየአመቱ በስደት የምታጣ ፣ ለቁጥር በሚታክቱ አሰቃቂ የመኪና አደጋዎች በየቀኑ ዜጎቿ የሚረግፉባት ፣ በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ዜጎቿ በህክምና እጥረት በሞት የምትነጠቅ ፣ ችግሮቿ ለቁጥር የሚታክቱ ነገር ግን ኩሩ ታሪክ ያላት ጥቂት ሆዳሞች በፈጠሩት ችግር አንገቷን የደፋች ሃገር ናት።
እነሱ ግን ልክ እንደማናውቃት ሌላ ሃገር ኢኮኖሚዋ አለምን ባስገረመ መልኩ ለተከታታይ ብዙ አመታት የተመነደገባት ፣  የአለማችን መዓት ሃገራት የሚቀኑባትና ልምድ የሚቀስሙባት ናት ይሉናል። ለመሆኑ ይህች እነሱ የሚሏት ሃገር የት ነው ያለችው? ለምን ይሆን ስለገዛ ሃገራችን ከአመት አመት ልክ እንደማናውቃት በሞኝ ውሸት የሚሰብኩን?
ሃገራችን ችግር ላይ መሆንዋን ችግርዋም ከግዜ ወደ ግዜ እየተወሳሰበ ለመፍታት ወደሚያስቸግር ሂደት ውስጥ እየገባ መሄዱን የተለያዩ ምሁራን ፣ ፖለቲከኞች ፣ ተንታኞች እንዲሁም አለማቀፍ ድርጅቶች ሲወተውቱ በአንፃሩ ደግሞ መንግስት ነኝ ብሎ የተቀመጠው አካል የዝሆን ጆሮ ይስጠኝ እያለ ነው። ሁላችንም የምናውቀው አንድ እውነት ከጥቂት ሆዳሞች በስተቀር ኢትዮጲያዊ ሆኖ ሃገር እንድታድግለት የህዝቡም ኑሮ እንዲሻሻልለት የማይፈልግ የለም። ነገር ግን መንግስት ተብየው የሃገራችንን ችግር ለመፍታት ከመሞከር ይልቅ የባሰ እያወሳሰበውና ጭርሱንም እየሸፋፈነ ወደ መፍትሄ አልባነት እየገፋው ይገኛል። የችግሩንም መኖር የሚጠቁሙ ዜጎችና አለማቀፍ አካላት እንደመንግስት ተቀራርቦ መፍትሄ ከመፈለግ ይልቅ እንደሃገር ጠላት እየፈረጀ ይገኛል።

ኖርዌይ ኢህአዴግ ያሰረባትን ዜጋዋን ጉዳይ እየተከታተለች ነው


ማዕከላዊ እስርቤት ከፍተኛ ስቃይ ይደርስባቸዋል በሚል ተሰግቷል

okello
የኢህአዴግን ካዝና የምትሞላዋ ኖርዌይ በማዕከላዊ እስር ቤት የሚገኙትን ዜጋዋን አስመልክቶ በዲፕሎማሲያዊ መንገድ እየሰራች መሆንዋ ታወቀ። በማዕከላዊ እስር ቤት የታሰሩት ዜጋዋ ድብደባና ቶርቸር እንዳይካሄድባቸው በቅርብ ክትትል እያደረገች መሆንዋን ለጉዳዩ ቅርብ የሆኑ ክፍሎች ለጎልጉል አስታውቀዋል።
ኢህአዴግን ከልጅነቱ ጀምራ ስትደጉም የኖረቸውና አሁን ደግሞ “በልማታዊ መንግሥትነት” መድባ ድጋፏን የምትዘረጋለት ኖርዌይ ዜጋዋን አስመልክቶ አስፈላጊውን ሁሉ የማድረግ ግዴታ እንዳለባት ይታወቃል። በዚሁ መሰረት የኖርዌይ ትልቁ ጋዜጣ ቀደም ሲልጎልጉል ምንጮቹን ጠቅሶ ይፋ ያደረገውን ዜና የሚያረጋግጥ ዜና አሰራጭቷል።
ደቡብ ሱዳን የጸጥታ ሃይሎች አሳልፈው ለኢህአዴግ የሰጧቸው የቀድሞ የጋምቤላ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦኬሎ አኳይ የኖርዌይ ዜግነት እንዳለቸው በማረጋገጥ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጉዳዩን በቅርበት እንደሚከታተለው፣ አዲስ አበባ የሚገኘው የኖርዌይ ኤምባሲም ስራውን እየሰራ እንደሆነ አፍተን ፖስት አመልክቷል።
አፍተን ፖስት “የሰብአዊ መብት ተከራካሪ” ሲል በዜናው መክፈቻ የጠቀሳቸውን አቶ ኦኬሎ አኳይን አስመልክቶ የውጪጉዳይ ሚኒስቴር የኮሙኒኬሽን አማካሪ ስቫይን ሚኬልሰንን ጠቅሶ “አቶ ኦኬሎ የደቡብ ሱዳን የደህንነት ሃይሎች በደቡብ ሱዳንና በዩጋንዳ ድንበር መካከል ይዘዋቸዋል። አንደተያዙም ወደ ጁባ ሳይወሰዱ ተላልፈው ተሰጥተዋል” በማለት የጉዳዩን አካሄድ አመላክቷል።

Thursday, April 3, 2014

ኢህአዲግ/ወያኔ ሕዝብ ለማፋጀት የገነባውን “የመርዝ ብልቃጥ”


ምርቃቱ የሩዋንዳው የዘር ማጥፋት ግጭት ከተጀመረበት 20ኛ ዓመት ጋር ገጥሟል

በአርሲ ዞን በሂቶሳ ወረዳ ከሃያ ሚልዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ያሰራውን  ''አኖሌ ሐውልት'' እና ሙዝዬም
ኢትዮጵያን እየመራ የሚገኘው ኢህአዲግ/ወያኔ የኢትዮጵያን ሕዝብ ከቀን ወደ ቀን እርስ በርሱ እንዳይተማመን፣ እንዲነቃቀፍ፣ እንዲጠራጠር ከእዚህ ባለፈ ደግሞ ግጭት እንዲፈጠር እያደረገ 22 ዓመታትን ዘለቀ። ህዝቡ እለት ከእለት በገዢው መንግስት የሚወጠኑለትን የእርስ በርስ ማጋጫ ተንኮሎች እየተመለከተ ልቦናው በእጅጉ እየደማ ነው።
አንድ ወራሪ የውጭ ጠላት ሊሰራ የሚችለውን ያህል ህዝብን ከሕዝብ ጋር የማጋጨት ሥራ ኢህአዲግ/ወያኔ በትክክል ሰርቶበታል። የሃገሪቱን ፌድራል አስተዳደር በየትኛውም ዓለም ያልታየ ቋንቋን መሰረት ያደረገ አስተዳደር ለኢትዮጵያ ደገሰላት። ፌድራላዊ አስተዳደር በዘመናዊው ዓለም አንዱ እና አማራጭ የአስተዳደር ዘይቤ ይሁን እንጂ በየትኛውም ሀገር መሰረት የሚያደርገው የመልክዓ ምድርን አቀማመጥ እና ታሪካዊ አሰፋፈርን ነው። እርግጥ ነው ጣልያን ሀገራችንን በወረረ ዘመን አሁን ወያኔ የሚጠቀምበትን የክልል አስተዳደር የመሰለ ቋንቋን መሰረት ያደረገ የአስተዳደር መዋቅር ዘርግቶ ነበር።
አንዳንዶች የአሁኑ ቋንቋን መሰረት ያደረገ አስተዳደር የብሔር ብሄረሰቦችን መብት ከማስከበር አንፃር የሚመስላቸው የዋሃን አይጠፉም። ግን ፈፅሞ አላማው ይህ ላለመሆኑ ብዙ ማስረጃ መጥቀስ ይቻላል።እርግጥ ነው የህዝብ ባህል ማለትም ቋንቋው፣ አለባበሱ፣ ታሪኩ ወዘተ ሊጠበቅለት እና ከለላ ማግኘት አለበት። ይህ ከለላ በማግኘት መብት  ስም ወንጀል ሲሰራ፣ ቁርሾ በባትሪ እየተፈለገ ሲራገብ እና ሕዝብን ከሕዝብ ለማጋጨት ሲውል ነው ወንጀሉ።
ኢህአዲግ/ወያኔ ሕዝብ እርስ በርሱ በጎሳ ሲጋጭ መፍትሄ ለመፈለግ ከመነሳት ይልቅ ጉዳዩን ሲያባብስ እና ቤንዚን ስያርከፈክፍ ማየት ለኢትዮጵያ ሕዝብ ዕለት ከዕለት የሚመለከተው ድራማ ሆኗል። ለእዚህም ብዙ አብነቶችን መጥቀስ ይቻላል። ለእዚህ ፅሁፍ ግን ሁለት ምሳሌዎችን እንጥቀስ -
  1. በዩንቨርስቲዎች ውስጥ ወጣቶች ‘አንተ የእገሌ ነህ አንተ የእንቶኔ ነህ’ ተባብለው ፀብ ሲነሳ ጉዳዩ የመጪው ትውልድ እና የአሁኑ ትውልድ አደገኛ አቅጣጫ ነው ብሎ የችግሩን ስር ለመፍታት ከመጣር እና የጉዳዩን አስከፊነት  በመገናኛ ብዙሃን ከመግለፅ እና ከማስተማር ይልቅ ፖሊስ ይልቁን ከአንድኛው ወገን ቆሞ ሌላውን ሲያስር እና ሲቀጣ መመልከት ዘግናኝ ተግባር ነው።
  2. ሕዝብ ለዘመናት ከኖረበት የእርሻ ቦታ ”የእገሌ ዘር ነህ” ተብሎ በክልል መስተዳድሮች ጭምር ሲባረር ለጉዳዩ እንደ መንግስትነት ለመዳኘት ሳይሆን የሚሞከረው እንደ ቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ አባባል ”ቀድመው ባልተወለዱበት ሀገር መስፈር የለባቸውም” እንደ አቶ አለምነህ የብአዴን ቢሮ ምክትል ኃላፊ ደግሞ ”የትዕቢት ልጋግ” ነው የሚሉ መልሶችን መስማት እራስ ያማል። መሪዎቻችን እንዲህ እያሉ ከጉርዳፈርዳ እስከ አሶሳ፣ ከአሶሳ እስከ ሐረር፣ ከሐረር እስከ ጅጅጋ፣ ከጅጅጋ እስከ ቦረና ጉጂ፣ ድረስ በብዙ አስር ሺህ የሚሆኑ ኢትዮጵያውያን በኢህአዲግ/ወያኔ የጎሳ ፖለቲካ ተሰደዱ፣ ተገደሉ። ይህ ሁሉ ሲሆን ግን መንግስት ጉዳዩን እንደ ትልቅ ችግር ሳይሆን እንደ አንድ የማስተዳደርያ ዘዴ እንደቆጠረው በ እርግጠኝነት መረዳት ይቻላል።