አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ - 53ኛ!!
በዓለማችን የሚገኙ የትምህርት ተቋማትን በማወዳደር ደረጃ የሚያወጣው (4 International Colleges & Universities (4icu)) የአፍሪካ ምርጥ የተባሉትን ዩኒቨርሲቲዎችን ዝርዝር ከጥቂት ሳምንታት በፊት አውጥቶ ነበር፡፡ ድርጅቱ በርካታ መረጃዎችን በመሰብሰብ እንዲሁም ለማንም ወገን ያላዳላ ጠለቅ ያለ ሒሳባዊ ትንታኔ በማድረግ ደረጃውን እንደሚያወጣ በድረገጹ ላይ ጠቁሟል፡፡
ከአንድ እስከ ሃያ ባሉት ዝርዝር ውስጥ የደቡብ አፍሪካና የግብጽ ዩኒቨርሲቲዎች ደረጃውን በብዛት ተቀራምተውታል፡፡ ታንዛኒያ፣ ናይጄሪያ፣ ዩጋንዳ፣ ቦትስዋና እና ኬኒያ እስከ ሃያ ባለው ደረጃ በመግባት የአገራቸውን የትምህርት ተቋማት ብቃት አስመስክረዋል፡፡
ከተመሠረተ 60ዓመታት ያለፉት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ (በቀድሞ ስሙ የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዩኒቨርሲቲ) እስከ መቶ ባሉት ዝርዝር ውስጥ የ53ኛ “ክብር” ተጎናጽፎዋል፡፡ ከተመሠረቱ ጥቂት ዓመታት በሆናቸው ዩኒቨርሲቲዎች ተበልጦ ለዚህ የበቃው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በቀደምት ዓመታት የበርካታ አፍሪካውያን ኩራት ነበር፡፡
ህወሃት/ኢህአዴግ ሎሌዎቹን ከየቦታው ሰብስቦ ሥልጣን በያዘ ማግስት መጀመሪያ የወሰደው እርምጃ ኢትዮጵያ በከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ያስተማረቻቸውን 42 ምሁራን በሁለት መስመር ደብዳቤ ማባረር ነበር፡፡ በአቶ መለስ ቀጥተኛ ትዕዛዝ ዶ/ር ዱሪ መሐመድ ያባረሯቸው እነዚህ ምርጥ ምሁራን እንደ ምሁርነታቸው በነጻ በማሰባቸውና ተማሪዎችንም እንደዚያው እንዲያስቡ በማድረጋቸው እንጂ በደብዳቤው ላይ እንደተገለጸው ተፈላጊ ባለመሆናቸው እንዳልነበር የታወቀ ነው፡፡
ኢህአዴግ ሥልጣን ከያዘ በየቦታው የፈለፈላቸው የካድሬ ማምረቻ “ዩኒቨርሲቲዎች” ስሙን ከመያዝ በስተቀር እስከ 100 ባሉት ዝርዝር አንዳቸውም ለመገኘት አለመብቃታቸው የኢትዮጵያን የትምህርት ጥራት ምን ደረጃ ላይ እንደደረሰ የሚያሳይ ነው፡፡