ህወሃት አባረረ፣ ብአዴንና ደኢህዴን ባሉበት ቀጠሉ
March 21, 2013 05:35 am By 1
Comment
“ስቱኮ” ግልብጥና ግጭት የበዛበት መኪና ተቀጥቅጦ አልስተካከል ሲል፣
የተገጣጠበና አልመሳሰል ያለ ግድግዳ “በግድ” ለማመሳሰል የሚያገለግል ቶሎ የሚፈረካከስ ጭቃ መሰል የቀለም አይነት ማጣበቂያ
ነው።
“ኮሚኒስቶች በችግርና በቅራኔ ውስጥ ሆነው በግድ ለመመሳሰል አንድ ዓይነት
መለያ መልበስ ይወዳሉ። ኢህአዴግም በተመሳሳይ በችግር ውስጥ ተዘፍቆ ሳለ፣ ለተመልካችና ለካሜራ ተመሳሳይ ልብስ ለብሶ በግድ
አንድ ነኝ ሲል ማየቱ ብዙም የሚገርም አይደለም” የሚለው አስተያየት በስፋት እየተሰጠ ነው። “በግድ አንድ” ሆነው በየክልሉ
ስብሰባ የሚያካሂዱት እህት ፓርቲዎች የለበሱትን መለያ የሚያመርተው ደግሞ የህወሃት የንግድ ድርጅት አልሜዳ ጨርቃጨርቅ እንደሆነም
ለማወቅ ተችሏል።
ባህር ዳር ላይ ለሚያካሂደው ጉባኤ በዝግጅት ላይ ያሉት “እህት” ፓርቲዎች
በየክልላቸው በስብሰባና በምርጫ ተጠምደው ሰንብተዋል። ውሉ ያልታወቀውና ምስጢር የተደረገው የኦህዴድ ጉባኤ የምርጫውን ውጤት
ማጠናቀቅ አልቻለም። ህወሃት በመተካካት ስም ነባሮቹን አራት አመራሮች ሲያሰናብት፣ አቶ በረከትና አዲሱ ለገሰ የኢህአዴግ
የመተካካቱ ስልታዊ በትር ሳይነካቸው ማለፉ ተደምጧል። ደኢህዴን በነበረበት እንደሚቀጥል ይፋ ሆኗል።
ኦህዴድን ለመምራትና ሰባት አመራር በሚሰየምበት የኢህአዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ
አባል ለመሆን አባ ዱላ ገመዳ፣ ግርማ ብሩ፣ ድሪባ ኩማ፣ ኩማ ደመቅሳ፣ አለማየሁ አቶምሳ፣ አስቴር ማሞና ደግፌ ቡላ ከተጠቆሙት
መካከል ይገኙበታል። የህወሃት የንግድ ተቋምና አንደበት የሆነው ሬዲዮ ፋና “የተጠቆሙትን አመራሮች ለማሳወቅ የድምጽ ቆጠራው ጊዜ
ስለሚወስድ ለነገ ተላልፏል” የሚል ዘገባ አሰራጭቷል።

