Wednesday, January 30, 2013

“የመበስበሱ በሽታ ሁሉም ዘንድ ነው”

ሻዕቢያው በረከት ህወሃትን ሊነዱት ይሆን?

bereket vs sebhat

የአቶ በረከት ስምዖንና የአቶ ስብሃት ነጋ የደፈጣ ውጊያ ገሃድ መውጣቱን የሚያመላክት መረጃ ይፋ መሆኑን ተከትሎ በህወሃት መንደር ውስጥ ከፍተኛ መደናገጥ ተፈጥሯል። ጉዳዩን የሚከታተሉ እንደሚሉት ልዩነቱን ለማርገብ በከፍተኛ ደረጃ ጥረት ቢደረግም ሊሳካ አልቻለም።

ከፍተኛ ስልጣን የያዙትንና አቶ መለስ ለመተካካት ያዘጋጇቸውን አዳዲስ አመራሮች፣ በቅርቡ ደንብና ህግ በመጣስ ሹመት የሰጡዋቸውን ጨምሮ የሰራዊቱን አዛዦችና ደህንነቱን ከጎናቸው ያሳተፉት ክፍሎች የተፈጠረው ልዩነት እልባት ማግኘት ይገባዋል የሚል አቋም መያዛቸውን የሚጠቁሙ ክፍሎች እነማን ተለይተው እንደሚመቱ ለመገመት አስቸጋሪ መሆኑንን ይገልጻሉ።

“ፓርቲያችን ከእንጥሉ በስብሷል” በማለት ከዛሬ አስራአንድ ዓመት በፊት በአገር ክህደት ሊያስወግዷቸው የተነሱትን ጓዶቻቸውን የረቱት መለስ የተጠቀሙበት ዋንኛ ስልት አባይ ጸሃዬን “ከውህዳኑ” ጋር በማሰለፍ ነበር። ዛሬ ለህወሃትና ለትግራይ ህዝብ በትግርኛ ቋንቋ ተጽፎ ተሰራጨ የተባለውና ይህንኑ መረጃ ዋቢ በማድረግ ኢየሩሳሌም አርአያ በተለያዩ ድረገጾች ይፋ እንዳደረጉት አቶ አባይ ጸሐዬ የተመደቡት ወጥመዱ ከተጠመደባቸው ዘንድ ነው።

“ድርጅትህ ኢህአዴግ እስከዛሬ ታግሎ እዚህ አድርሶሃል። በተለይም የሁሉም ነገር አድራጊና ፈጣሪ የሆነው ባለ ራዕዩን መሪህን በቅርቡ አጥተሃል” የሚል የአምልኮ መሪ ቃል ያለበት የጥሪ ወረቀት “ተቆርቋሪ ለሆናችሁ የትግራይ ተወላጆች በሙሉ” በማለት ጥሪ አቅርቧል። ኢየሩሳሌም አርአያ ቃል በቃል በትምህርተ ጥቅስ አኑረው ባሰራጩት በዚህ ጉልህ ዜና “እነ አቶ በረከት፣ ወ/ሮ አዜብ፣ ቴዎድሮስ ሃጎስ” ወረቀቱን አዘጋጅተው እንዳሰራጩ ያስረዳል።

በኢየሩሳሌም አርአያ ዜና ላይ እንደተመለከተው እነ አቶ ስዩም መስፍን፣ አባይ ጸሐዬ፣ አለቃ ጸጋዬ ከነባለቤታቸው የትግራይን ህዝብ ለጠላት ለመስጠት በዝግጅት ላይ መሆናቸውን ያወሳል። “… የኔ የምትላቸው ጅቦች ተነስተውብህ ይገኛሉ” የተጠቀሱትንና ሌሎች ደጋፊዎቻቸውን “ጅቦች” ሲል የሚጠራው መልዕክት፣ “… ከእኛ ኋላ የተፈጠሩና ራሳችን ያሳደግናቸው ሲጠናከሩ ድርጅታችን ግን እየተዳከመ በመሄድ ላይ ነው” ሲል ያሳስባል። እነማን እንደሆኑ በግልጽ ሳይዘረዘር “የተወገዱ ግን በመጥፎ ጎዳና ያልተሰማሩን መልሰን ወደ ፓርቲው ማስገባት አለብን። ይህ ካልሆነ ግን የህዝብ ትግል አውላላ ሜዳ ላይ ጅብ በልቶት ሊቀር ነው ከጠላቶቻችን ጋር እንታረቅ እያሉን ነው” የሚል ማስጠንቀቂያ ያስቀምጣል። በስተመጨረሻ “ከጀርባ ሆኖ የዚህ አፍራሽ ዋና ቀያሽ መሃንዲስ ስብሃት ነጋ መሆኑን ደርሰንበታል” ይላል።

Tuesday, January 29, 2013

እግርኳሳችን የራሷን ሙሴ ትፈልጋለች

 

game

ስሜት ጎርፍ ነው፤ ያውም ደራሽ ጎርፍ፤ ብሄራዊ ቡድናችንን ስንደግፍም ሆነ ስናወድስ እንዲሁም ስንወቅስ በዚሁ ደራሽ ጎርፍ መወሰዳችን ይታያል። ይሄ ችግር ግን እንደ ሃገርም ችግራችን እየሆነ የመጣ ነገር ነው በስሜት መደገፍ በስሜት መቃወም፤ ዛሬ ያወደሱትን ነገ መርግም ሁሉንም ነገር በዘላቂ ጥቅም፤ በዘላቂ ስራ እና በዕውቀት መመዘን እያቃተን ነው። ከዚያም ዐልፎ ስሜታችን ጫፍ ላይ በሚደርስበት ጊዜ ሰከን ብሎ የሚያስብ ሰው ሲያጋጥመን እንደጭራቅ እንመለከተዋለን። ከእኛ በሓሳብ የተለየ አስተያየት የሰጠ እንደሆነማ በቃ ቤተክርስቲያን ውስጥ የገባ ውሻ እናደርገዋለን።…

የሰሞኑ የብሄራዊ ቡድናችን ውጤትም የዚህ ጎርፍ ሰለባዎች መሆናችን አንዱ ማሳያ ነው። መጀመሪያ ላይ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አዲስ አበባ ከቤኒን ብሄራዊ ቡድን ጋር ሲጫወት አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የአሰላለፍ ስህተት ሰርቶአል መሃል ላይ ምንም ፈጣሪ /creative/ ተጫዋች አልነበረውም በሚል ከውጤቱ በኋላ ህዝቡም ጋዜጠኞችም ሲያወግዙት ከረሙ። ልብ አድርጉ እዚህ ጋር ሁሉም የሚያወራው በስሜት የዕለቱን ጨዋታ በተመለከተ የነበረውን ችግር እንጂ በዕውቀት የሃገራችን እግርኳስ ችግር ምንድን ነው? ብሎ ስለዘለቄታው የሚያወራ እና የሚያስብ የለም። ፌደሬሽኑም ቢሆን ህልውናውን ከጊዜያዊ ውጤት ጋር አጣብቆ የተቀመጠ ስለሆነ ዘለቄታዊ ስራ ሲሰራ አይታይም እናም አቶ ሰውነት ያቺን የተችት ፍላጻ እንደምንም ሽል ብለው አሳለፏት ። …

ቀጥሎም ከጥቂት ጊዜያት በኋላ ሱዳንን አሸንፈን ለአፍሪካ ዋንጫ አላፊ መሆናችንን አረጋገጥን፤ ስሜት አሁንም እንደደራሽ ጎርፍ አጥለቀለቀን ህዝቡ ”ሳላዲን ጥቁር ሰው” ተባለ። ሲሰደብ የነበረው ሰውነት በየኤፍኤም ራዲዮው ጋሼ ጋሼ መባል ተጀመረ። አንዳንዶቹም ኢትዮጵያዊው ሞሪኖ ይሉት ጀመር። አሁንም እዚህ ጋር ረጋ ብሎ በዕውቀት ይሄ ውጤት ጊዜያዊ ነው፤ ዘለቄታዊ ውጤት የምንፈልግ ከሆነ ሰከን ብለን የእግርኳሱን ችግር እንመልከት በስሜት አንነዳ የሚል ሰው ሲገኝ እንደከሃዲ ሃገሩን እንደማይወድ ተቆጥሮ መወገዝ ጀመረ በስሜት! አቶ ሰውነትም ይህቺን ስለሚያውቅ በሴካፋ ውድድር መሳተፋችን አስፈላጊ አይደለም ብሎ ራሳችንን ከሴካፋ ውድድር እንድናገልል አደረገ። ለምን? ምክኒያቱም ስሜታዊ መሆናአችንን ስለሚያውቅ በሴካፋ ላይ የሚመጣው ውጤት የእርሱን ከብሄራዊ ቡድን ጋር ቆይታ ስለምትወስን ቁማሩን መቆመር አልፈለገም። አዎ ስራዎች በዕቅድ እና በዕውቀት ሳይሆን በስሜት በሚሰሩበት ሃገር ለምን ሪስክ ይወስዳል? …

Saturday, January 19, 2013

አሜሪካ በአፍሪካ ወታደራዊ የበላይነቷን ልታረጋግጥ ነው!

ፕሮግራሙን ለማስፈጸም 35 አገሮች ተመርጠዋል

 

africom 1

January 19, 2013 03:40 am By Leave a Comment

አዲስ በተያዘው የአውጳውያን ዓመት አሜሪካ በአፍሪካ ከፍተኛ ወታደራዊ የበላይነትን ሊያረጋግጥላት የሚችል ፕሮግራም ነድፋለች፡፡ ከሦስት ሳምንታት በፊት ይፋ የሆነውን ፕሮግራም ተግባራዊ ለማድረግ በሚያስችል ሁኔታ ላይ የተነደፈውን ዕቅድ የሚያስፈጽሙ 35 የአፍሪካ አገሮችም ተመርጠዋል፡፡

ምንም እንኳን ዜናው ይፋ ከሆነ የቆየ ቢሆንም የአሜሪካንን የመከላከያ ሚኒስቴር (ፔንታጎን) እንዲመሩ የታሰቡት ሪፓብሊካኑ ቸክ ሔግል ቀዳሚ ተወዳዳሪ መሆናቸው እስከሚገለጽ ድረስ የብዙዎችን ቀልብ አልሳበም ነበር፡፡ የአሜሪካንን ጦር ሠራዊት በየአገሩ በማዝመት ጉዳይ ላይ ጽኑ የተቃውሞ አስተሳሰብ የሚከተሉት ሔግል እንዲህ ዓይነቱን ፕሮግራም ለማስፈጸም ገጣሚ ሚኒስትር እንደሚሆኑ በሰፊው እየተነገረ ነው፡፡

የመከላከያ ሚኒስቴር መ/ቤቱ ይፋ እንዳደረገው በአፍሪካ በየጊዜው እያገረሸ የሄደውን የአሸባሪዎች እንቅስቃሴ ለመቆጣጠርና ሌሎች በክፍለ አህጉሩ የሚነሱ ቀውሶችን ለመከላከል የሚል ዕቅድ የወጣለት ፕሮግራም በያዝነው የአውሮጳውያን ዓመት ተግባራዊ ይሆናል፡፡ ይህ በዓይነቱ የመጀመሪያ የሆነው ፕሮግራም የሚያተኩረው ጦርነት ወይም ሁከት በተፈጠረ ጊዜ የአሜሪካንን ወታደሮች በየቦታው ከመላክ ይልቅ አፍሪካውያንን ለራሳቸው ችግር ወታደራዊ ዕርምጃ ለመውሰድ እንዲችሉ የሚያደርግ ነው፡፡ ይህንንም ተግባራዊ ለማድረግ እንዲያስችል የአሜሪካ ወታደራዊ መኮንኖች ለአፍሪካውያኑ የተለያየ ወታደራዊ ሥልጠና ለመስጠት ወደዚያው ያመራሉ፡፡

Wednesday, January 16, 2013

“በ2030 ከሚከሽፉ መንግሥታት አንዷ ኢትዮጵያ ነች”

ዘገባው የ15 አገራትን ዝርዝር አውጥቷል

 

NIC 1

የአሜሪካ የብሔራዊ የደኅንነት ምክርቤት እንደ አውሮጳውያን አቆጣጠር በ2030 የሚከሽፉ 15 መንግሥታትን (failed states) ዝርዝር አውጥቷል፡፡ “በግጭት መብዛትና በአካባቢ ጥበቃ ቀውስ ምክንያት” ይከሽፋሉ ተብለው ከተተነበዩት የአፍሪካ፣ የእስያና የመካከለኛው ምስራቅ አገራት መካከል ኢትዮጵያ አንዷ ነች፡፡

እጅግ የነጠረ፣ ያልተዛባና የተጠና ዘገባ ለአሜሪካ የስለላ ተቋማት፣ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ አውጪዎችና ለዓለምዓቀፍ ግንኙነት ተመራማሪዎች በማውጣት የታወቀው የአሜሪካ ብሔራዊ የደኅንነት ምክርቤት ከተቋቋመ በርካታ ዓመታትን አስቆጥሯል፡፡ ምክርቤቱ በሚያወጣቸው ዘገባዎች የአሜሪካ መንግሥትም ሆነ የተለያዩ መ/ቤቶች ተጽዕኖ እንደማያደርጉበት የሚናገር ሲሆን፤ ዘገባዎቹንም ከአድልዎ እና ከአሜሪካ መንግሥት አቋም ነጻ በመሆን እንደሚያዘጋጃቸው ይናገራል፡፡

የም/ቤቱ ዘገባ በተለይ ምርጫ ከተካሄደ በኋላ ለመጪው ፕሬዚዳንት የወደፊቱን የዓለማችን መልክ ምን እንደሚመስል የመካከለኛና የረጅም ጊዜ ስትራቴጂካዊ አስተሳሰቦች እና ዓለምአቀፋዊ ዝንባሌዎች ላይ አቅጣጫ የሚጠቁም ትንበያ ያደርጋል፡፡ ለፕሬዚዳንቱ ዓለምአቀፋዊ የደኅንነት ዘገባ ያቀርባል፤ ለብሔራዊ የጸጥታ ምክርቤት እና ለአገር ውስጥ ደኅንነት መ/ቤት ምክር ያቀብላል፤ በአጠቃላይ የአሜሪካን የስለላና የደኅንነት ማኅበረሰብ ሊከተል በሚገባው ጉዳይ ላይ አቅጣጫ የሚያስይዝ ሃሳብ ያቀርባል፡፡

በዚሁም መሠረት ባለፈው የታህሳስ ወር “በ2030 የዓለም አቅጣጫ፡ አማራጭ አገራት” በሚል ርዕስ አንድ ዳጎስ ያለ ጥናት አቅርቧል፡፡ ይኸው 160ገጽ ያለው ዘገባ የዛሬ 17ዓመት የዓለማችን ገጽታ ምን እንደሚመስል ከየአገራቱ በተወሰደ ጥናትና እዚያው በሚገኙ ተመራማሪዎች የሰበሰበውን ያካተተ ነው፡፡ ዓለማችን የምታዘነብልባቸው ቀዳሚ ሁኔታዎች አንዱ ሰዎች በራሳቸው አነሳሽነት ድህነትን ለመቀነስ፣ በትምህርት ለማደግ፣ በቴክኖሎጂና በህክምና ለመራቀቅ እንዲሁም በገቢም የመካከለኛው መደብ ላይ ለመድረስ የሚያደርጉት ጥረት በከፍተኛ ሁኔታ ከተጠቀሱት አንዱ አቅጣጫ ጠቋሚ ነው፡፡

Friday, January 11, 2013

“በህወሓት ተወርረናል!” ደቡብ ሱዳኖች

ኃያልነታችን ብሔራዊ ይሁን

 

tplf and south sudan

አዲሷ አገር ደቡብ ሱዳን እንደ መንግሥት ተመቻችታ አልቆመችም። የፋይናንስ ስርዓቱም የተረጋጋ አይደለም። የገቢና ወጪ ቁጥጥሩ ክፍተት ያለበት በመሆኑ ለሙስና የተጋለጠ ነው። የጁባ ነዋሪዎች እንደሚሉት ከሆነ የአገሪቱ ሃብት በግለሰቦች እጅ ነው። በተለያዩ መስኮችም የባለሙያና የአቅም ችግር አገሪቱ ምስጢርና የኔ የምትለው አስተዳደር እንዳይኖራት አድርጓታል የሚሉ በርከቶች ናቸው።

ይህንኑ ክፍተት ለመሙላት በሚል ኢህአዴግ ደቡብ ሱዳንን ከተወዳጀ ጀምሮ ከፍተኛ ድጋፍ ሲያደርግ ቆይቷል። የመከላከያ መኮንኖችን አሰልጥኗል፤ የፖሊስ ኃይሉን አደራጅቷል። በአማካሪነት በተለያዩ ዘርፎች የራሱን ሰዎች ጠቅጥቆ አሁንም ይህንኑ ድጋፉን አጠናክሮ ቀጥሏል። የተመሰረተው ግንኙነት ወደፊትም እንዲሁ በቀላሉ ንፋስ የሚገባው አይመስልም። ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው እንደሚሉት ኢህአዴግ በህወሃት አማካይነት ደቡብ ሱዳንን ጠፍንጎ የያዘበት ሰንሰለት በቀላሉ ሊበጠስና ሊሸረሸር የሚችል እንዳልሆነ ይናገራሉ።

ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁ እነዚሁ በጁባ የሚኖሩ ክፍሎች በፋይናንስ፣ በፖሊስ፣ በመከላከያ፣ በደህንነት፣ በተለያዩ ከፍተኛ ግዢዎችና በገንዘብ ዝውውር በኩል የደቡብ ሱዳን ማናቸውም እንቅስቃሴ ከኢህአዴግ እይታና ክትትል ውጪ አይደለም። እንደ አገር ኢትዮጵያ በቀጠናው ኃያል መሆኗ ቢያስደስትም አሰራሩ “ህወሃት በኢትዮጵያ ስም፣ የህወሃት ልጆች በኢህአዴግ ስም” መከናወኑ ቅሬታ ፈጥሯል።

“ብሔራዊ ጥቅምን በብሔራዊ አጀንዳ ማስጠበቅና ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ማስኬድ ኩራቱ የሁሉም ዜጎች እንዲሆን ያደርገዋል” የሚሉት ክፍሎች በተግባር የሚታየውና በብሔራዊ ስም የሚከናወነው ስራ “ህወሃትና የህወሃት ሰዎች በብቸኛነት እንዲጠቀሙበት የሚያደርግ ነው፤ ሕዝብ የወከለውና የራሱን አገር ጥቅም የሚያስከብር አስተዳደር በኢትዮጵያ ላይ እስከለሌለ ድረስ አካሄዱን ብሔራዊ ወይም የአገር ኩራት ለማለት አይቻልም” ብለዋል። አያይዘውም ኃያልነታችን በብሔራዊ ደረጃ እንጂ በድርጅትና በጎሣ ደረጃ መሆን የለበትም በማለት ይከራከራሉ፡፡ ሲያስረዱም በብሔራዊ ሽፋን ለመበልጸግ የሚደረግ ሩጫ ዓቅምን ካላገናዘበው የኤርትራ ፍላጎትና በውጤቱም ከጎረቤት ሁሉ ጋር ከጠብ እስከ ዓይነቁራኛ መተያየት ከመድረስ ጋር ልዩነት አይኖረውም ይላሉ፡፡

ከ33ቱ የአዳማ ፔቴሽን ፈራሚ ፓርቲዎች የተሰጠ መግለጫ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የምርጫውን ሂደት እየገፋ ያለው ለገዢው ፓርቲ ብቻ በተመቻቸ ሜዳ ነው!

 

petition

በምርጫ አስፈፃሚው፣ ከምርጫ አስተዳደርና በምርጫው ሂደት ላይ የሚታዩ መሠረታዊ ችግሮችን በማንሣት ችግሮቹ ስለሚፈቱበት መንገድ የውይይት /ምክክር/ መድረክ እንዲመቻች ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድና ለመንግሥት አካላት ጥያቄአችንን ማቅረባችን ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የማያሣምኑ ምክንያቶች በመስጠት ጥያቄዎቻችንን ሙሉ በሙሉ ውድቅ ማድረጉን በቃል የገለፀልን ሲሆን ለመንግሥት ላቀረብነው ጥያቄ ምላሹን እየተጠባበቅን ነው፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ የተጣለበትን የአገርና የሕዝብ ኃላፊነት ወደጐን በመግፋት ምርጫውን ሠላማዊ፣ ዲሞክራሲያዊ፣ ነፃና ፍትሐዊ ምርጫ ለማድረግ የመወዳደሪያ ሜዳውን ከማስተካከል ይልቅ የገዢው ፓርቲ ወገንተኝነቱንና ጉዳይ ፈፃሚነቱን ባረጋገጠበት አቋሙ በመግፋት ወደ ምርጫ እንቅስቃሴ መግባቱን በይፋ አውጇል፡፡

እኛ በያዝነው ሠላማዊ የትግል መሥመር በምርጫ የመሣተፍ /አለመሳተፍ ጉዳይ ጥያቄ ውስጥ የሚገባ ያለመሆኑንና የሕዝብ ዘርፈ ብዙ ውስብስብ ጥያቄዎች ምላሽ የምንሰጥበት ብቸኛው የመንግሥት ሥልጣን መያዣ መሣሪያችን መሆኑን በተደጋጋሚ በግልጽ አስቀምጠናል፡፡ የአካባቢ ምርጫ ወደ ሕዝቡ ዘልቆ ለመድረስ የሚያስችል እንደመሆኑ ከአገር አቀፍ ምርጫ ያነሰ ትኩረትና ቦታ የምንሰጠው አይደለም፡፡ ይልቁንም ለምንፈልገው የሥርዓት ለውጥና የዲሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ መሠረቱ የሚጣለው በሕዝቡ ውስጥ ስለሆነ ለዚህ ምርጫ ተገቢውን ትኩረት ሰጥተን ጠንክረን ለመንቀሳቀስ ዝግጅታችንን በተባበረና በተቀናጀ መንገድ ለማድረግ እየተንቀሳቀስን ባለንበት ነው የጋራ ጥያቄዎቻችንን ያቀረብነው፡፡ ይሁን እንጂ ምርጫ ቦርድ በኢህአዴግ እየተመራና እየታገዘ ከጊዜ ሰሌዳ በፊት በመሠረታዊ ጉዳዮች ላይ መወያየት ይቅደም በማለት 41 የፖለቲካ ፓርቲዎች በአዳማው ስብሰባ ላይ ላቀረብነው የቦርዱ ሰብሣቢ “የውይይት መድረክ ይዘጋጃል” በማለት የመለሱትን፣ እንዲሁም 33 በሕጋዊና ሠላማዊ መንገድ የምንታገል የፖለቲካ ፓርቲዎች ፔቲሽን ፈርመን ላቀረብነው የቦርዱ ጽ/ቤት ኃላፊ “ባትጠይቁንም ማድረግ ያለብን ነው” “. . . ጉዳዩን ሣታጮሁት በትዕግሥት ጠብቁ” ማለታቸውን ክደው ከአዳማ በተመለሱ በ4ኛው ቀን አፀደቅን ባሉት የጊዜ ሰሌዳ ገፍተውበታል፡፡

Thursday, January 10, 2013

ይድረስ ለፈጣሪ!


(አሥራደው ከፈረንሳይ)
Where is God - Suffering
January 10, 2013 09:07 am By  Leave a Comment
ተጣፈ ተኔ «ወተህ ወርደህ የላብህን ወዝ ትበላለህ» ብለህ ወደ መሬት ከላከው የአዳም የልጅ፤ ልጅ፤ ልጅ፤ ልጅ፤ ልጅ፤ … አንዱ፤ ላንተ በሰማዬ ሰማያት ላለኸው አምላክ::

እነሆ ይችን ደብዳቤ በመልክተኛህ በመላኩ ገብርኤል በኩል ላንተ ስልክ፤ ካገኘህ ለራስህ በእጅህ እንዲሰጥ፤ ካጣህም ለእናትህ ለወላዲት አምላክ፤ እንዲሰጣትና እሷ እንድትሰጥህ አደራ ብዬዋለሁ::

አምላክ ሆይ !
ከጭቃ አድቦልቡለህ የፈጠርከው ሰውን ያህል ጨካኝ ፍጡር አንቱ እያልኩ፤ አንተን አንቱታ በመንፈጌ ከድፍረት እንደማትቆጥርብኝና ቁጣህ እንደማይበረታ አውቃለሁ፤ አንተታዬ የመውደዴና ላንተ ያለኝ የክበር መግለጫ መሆኑን አንተው ታውቃለህና!

ይኸውልህ ጉዳዩ እንዲህ ነው:
ፈጣሪ በጆሮው ላይ ተኝቶ የሕፃናትን ለቅሶ፤ የዕናቶችን ዋይታ፤ ያባቶችን ጣር፤ አልሰማ ብሏል፤ … ሕዝብ መከራው በዝቶ፤ የበደል ገፈቱ ገንፍሎ እየፈሰሰ፤ ዋይታውና ለቅሶው እንደ እሳተ ጎሞራ ላንቃውን ከፍቶ፤ የሰማዩን በር ሲለበልብ፤ ጮኸት በርክቶ፤ ፈጣሪ አልሰማ አለ::

Tuesday, January 8, 2013

“በፍቅርና በመተሳሰብ የምንኖርባት ኢትዮጵያ ትናፍቀኛለች”


(አንዷለም አራጌ)

andualem aragie
January 8, 2013 06:06 pm By  Leave a Comment
የአንድነት ፓርቲ አመራሮችና አባላት ከአንዷለም አራጌ ጋር ተገናኙ
“ከእስረኞች ሁሉ ህገ-መንግስታዊ መብቴ ተጥሶ ዘመድ አዝማድ እና ጓደኛ እንዳይጠይቀኝ የተደረኩት እኔ ነኝ” አንዷለም  አራጌ

የገናን በዓል ምክንያት በማድረግ የአንድነት ፓርቲ ከፍተኛ አመራር የነበረውንና በሽብርተኝነት ሰበብ ለእስር ተዳርጎ የሚገኘውን ወጣቱን ፖለቲከኛ አንዷለም አራጌን ከአንድነት ከፍተኛ አመራሮችና አባላት የተውጣጡ ሰዎች ጠይቀውት መመለሳቸውን የሕዝብ  ግንኙነት መረጃ ይጠቁማል፡፡ በዋናው መጠየቂያ በር አትገቡም ከተባለ በኋላ ወደ ማረሚያ ቤቱ አስተዳዳሪ የቀረቡት ጠያቂዎቹ ስም ዝርዝራቸው ከተመዘገበ በሁዋላ ሊፈቀድላቸው የቻለ ሲሆን ከወጣቱ ፖለቲከኛ አንዷለም አራጌ ጋር የማረሚያ ቤቱ ጠባቂዎች አጠገብ ቢኖሩም ውይይት አካሂደዋል፡፡

ከአንድነት ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች መካከል ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፣ የተከበሩ አቶ ግርማ ሰይፉ፣ አቶ ተመስጌን ዘውዴ፣ አቶ ዘካርያስ የማነብርሃን፣ አቶ ዳንኤል ተፈራ እና አቶ  ሙላት ጣሰው እና ከአስር በላይ የሚሆኑ አባላትም በመገኘት የአንዷለም የጤና ሁኔታና የእስር አያያዝ ምን እንደሚመስል ጠይቀዋል፡፡

Monday, January 7, 2013

ኢህአዴግ የውጭ ምንዛሪ አሰሳ ሊያካሂድ ነው



ዶላር አምራቾቹና ሰብሳቢዎቹ እነማን ናቸው?
Currencies
January 7, 2013 11:06 am By  1 Comment
ኢህአዴግ የተጭበረበረ የውጪ ምንዛሪ በማተምና በማሰራጨት ስራ የተሰማሩ እንዳሉ ከበቂ በላይ መረጃ ቢኖረውም ርምጃ እንደማይወስድ መደመጥ ከጀመረ ቆይቷል። በስራ ሽፋን የተጭበረበረ ዶላር የሚያትሙ የውጪ አገር ሰዎችን አስገብተው የሚሰሩት ለራሱ ለህወሃት የቀረቡ ሰዎች ዝርፊያ ስለማካሄዳቸው ፖሊስ ተደጋጋሚ መረጃ ቢደርሰውም ርምጃ ሲወስድ አይታይም በሚል የሚወቅሱት ጥቂት አይደሉም።

ቀደም ሲል የተጭበረበረ ዶላር የሚያስገቡ እንደነበሩ የሚገልጹት የጎልጉል የፖሊስ ምንጮች እነዚሁ ክፍሎች አቅማቸውን በማሳደግ የሐሰት (ፎርጂድ) ዶላር አገር ውስጥ ማተም ከጀመሩ ቆይተዋል። ከሩቅ ምስራቅና “ከትንሿ ታላቅ አገር” ህገወጥ ብር አታሚዎችን ከማሽን ጋር በማስገባት የአዲስ አበባን ሃብታሞች ሙጥጥ አድርገው ዘርፈው አድራሻ የቀየሩ አሉ። በዚህ ስራ ውስጥ ተሳታፊ ከሆኑት መካከል የህትመት ሰዎችም እንደሚገኙበት ጥቆማ አለ።

የለፉበትንና በብድር ያገኙትን ገንዘብ በሚያምኗቸው ትልልቅ ሰዎች ደላላነት በተጭበረበረ ዶላር ቀይረው የከሰሩ ጉዳዩን ወደ ክስ እንዳይወስዱ ራሳቸው የህገወጥ ስራ ተባባሪ መሆናቸው ያግዳቸዋል። ህግ ፊት እንዳይሄዱ ህገወጥ መሆናቸው የያዛቸው እነዚህ ስግብግቦች ባዶ እጃቸውን አጨብጭበው ለመቀመጥ ተገደዋል። ኃይል ለመጠቀም እንዳይሞክሩ ደላላ ሆነው የሚቀርቡት “ትልቅ” የሚባሉት የዘመኑ ሰዎችና ባለጊዜዎች መከታና ደጀን ስላላቸው ቀላል አይሆንም።

አይ.ኤም.ኤፍ. በሚባል ምህጻረ ቃል የሚታወቁት የኤ.ዲ.ኤች. ዋናሥራአስኪያጅና ባለአክሲዮን አቶ አየለ ደበላ፣ የአያት የመኖሪያ ቤት ድርጅት ሊቀመንበርና ዋና ባለአክሲዮን አቶ አያሌው ተሰማ፣ ጃማይካና ሌሎች አራጣ አበዳሪዎቸ “አራጣ በማበደር በባንክ ስራ ገብታችኋል” ተብለው በቁጥጥር ስር ሲውሉ፣ በተመሳሳይ መንግስት የተጭበረበረ ዶላር በማምረት ዝርፊያ ላይ የተሰማሩትና በየስርቻው እየገቡ ዶላር የሚያስለቅሙት እነማን እንደሆኑ መረጃው እንደነበረው ባልደረባችን ከአዲስ አበባ ያሰባሰበው መረጃ ያመለክታል።

Saturday, January 5, 2013

ቴሌን ደህና ሰንብት?


ዶ/ር ደብረጽዮን “አልረካንም” አሉ
ethiotelecom
January 5, 2013 03:39 am By  Leave a Comment

የቀድሞው የኢትዮጵያ ቴሌኮሙኒኬሽን ኮርፖሬሽን ስሙን ቀይሮ “ኢትዮቴሌኮም” በሚል ከተሰየመ በኋላ አስተዳደሩን ለፈረንሳዩ ፍራንስ ቴሌኮም ማስረከቡን ተከትሎ ኢህአዴግ ለወደፊቱ ያቀደውን እቅድ ይፋ የሚያደርጉ መረጃዎች ለንባብ በቅተዋል። በዛሬው እለት የመገናኛና የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር ዶ/ር ደብረጽዮን ገ/ሚካኤል “ቴሌ ከዚህ በኋላ ለውጪ ካምፓኒ አይሰጥም። በአገር ውስጥ ባለሙያዎች ይቀጥላል” ሲሉ የማሳረጊያ ንግግር አሰምተዋል። የሚኒስትሩን ንግግር ያደመጡ “ቴሌን ህወሃት ጠቀለለው” የሚል አስተያየት ሰጥተዋል።

የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ “አዲሱ ቴሌና ኢንሳ” በሚል ርዕስ ከወራት በፊት ለንባብ ባበቃው ጥናታዊ ጽሁፍ እንዳስታወቀው ቀደም ሲል “አዲሱ ቴሌ” በሚል አሮጌው ቴሌን የሚረከቡ የህወሃት ሰዎች የበዙበት፣ ለማዛነቂያ ከተለያዩ ብሄሮች በጣም ጥቂት ተተኪዎችን በማካተት ስልጠና ሲያካሂድ ነበር።

በህወሃት ሰዎች የሚመራውን የብሄራዊ መረጃና ደህንነት ተቋም (NISS) ዘመናዊ ለማድረግ ኢንሳን ሲያቋቁም ዋናው ዓላማው ከቴሌ ጋር በማቆራኘት ነበር። በጥናቱ እንደተገለጸው አሮጌው ቴሌ ውስጥ ያሉት አገር ወዳዶች ለተፈለገው የስለላ ስራ የሚታመኑ ባለመሆናቸው ሰራተኞቹን በሲቪል ሰርቪስ ማሻሻያ ስም ተጠራርገው እንዲወጡ ተደርጓል።
የፈረንሳይ ቴሌኮም ቴሌን እንዲረከብ ስለመደረጉ “ህወሃት አዲሱ ቴሌ በሚል እያሰለጠነ ያዘጋጃቸው የራሱ ሰዎች አሮጌውን ቴሌ ባደባባይ እንዲረከቡ ማድረግ የሚያስነሳውን ተቃውሞ በጥራትና በአገልግሎት ኋላቀርነት እንዲሁም በውጪ ካምፓኒ አሳብቦ ለመስጠት የማመቻቸት ስራ ለመስራት” መሆኑ አካሄዱ የገባቸው የቴሌ የበላይ ሃላፊዎች ውስጥ ውስጡን የሚያወሩት ጉዳይ ነበር።

Friday, January 4, 2013

አዲሱ የሃይማኖት ህግና የሃገሪቱ ህገመንግስት



constitution and religion
January 4, 2013 11:37 am By  Leave a Comment
አዲሱ የሃይማኖት ህግና የሃገሪቱ ህገመንግስት (በሰለሞን)

መንግሥት ሕገ-መንግስቱን ሊያከበር ይገባል! (ከእምነት ቤቶች)

በጉዳዩ ላይ እንድንወያይ ስንጠየቅ ይህ  የሃገረቱን ህገመንግስት ይቃረናል እኛም እዚህ ተወክለን የመጣነው ለሌላ ጉዳይ እንጂ በህግ ላይ ህግ ለማውጣት አይደለም ብለን አጀንዳው እንዲመለስ አድርገናል ፡፡(ከተስብሳቢዎች አንዱ)
በስራ ላይ የዋለውን እንደ አዲስ ለማጸደቅ በተዘጋጀው ረቂቅ ላይ ውይይት እንዲደረግ የእምነት ተቌማት የጋራ ጉባኤ ላይ ቀርቦ ነበር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ አይመለከተኝም ብላ ወጥታ ነበር ቀጥሎም የኢትዮጵያ እስልምና ጽህፈት ቤትም አይመለከተኝም ብሎ ነበር፡፡ በመጨረሻምወንጌላዊያን ይህ ህግ እነርሱ ላይ ተፈጻሚ ሆኖ የቆየ ቢሆንም በህግ መልክ እንደገና ሲቀርብ ግን ተገርመውበታል፡፡
“ኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች መርጠው በላኳቸው ተወካዮቻቸው አማካይነት ሕዳር 29 ቀን 1987 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ሕገ መንግስትን በአዋጅ ቁጥር 1/1987 ያጸደቁት” ሕገ መንግሥትን መንግሥት በተለያዩ ጊዜያት እየጣሰ መሆኑን የሀገሪቱ የተለያዩ ህብረተሰቦችና ተቋማት መናገር ከጀመሩ ሰነባብተዋል፡፡
በቅርቡ ደግሞ “በፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር የተዘጋጀ የሃይማኖት ድርጅቶች እና ማኅበራትን” አስመልክቶ የወጣው “መመሪያ” የተጠቃሻቹ የሃይማኖት ድርጅቶች እና ማኅበራትን በበቂ ሁኔታ ሃሳባቸው ሳይሰማና በማያውቁት ሁኔታ ሥራ ላይ በማዋሉ ምክንያት የሃይማኖት ድርጅቶችና ተቋማትን  በተለይም ደግሞ የክርስትና እምነት ተከታዩ ኅብረተሰቡን በእጅጉ የማጉረምረሚያ ሃሳብ ከመሆን አልፎ መንግሥት መመሪያውን በድጋሚ እንዲያስብበት በመጠየቅ ላይ ይገኛሉ፡፡

Wednesday, January 2, 2013

የማፍረስ አባዜ



"መካብ ሲያቅት ማፍረስ ሥራ ይሆናል"
atkilt tera


በአለፉት ሃያ አንድ ዓመታት፣ በተለይም ከ1997 ዓ.ም. ወዲህ፣ የወያኔ/ኢሕአዴግ አገዛዝ ልዩ መታወቂያው ያደረገው  እያፈረሱ መገንባትን ነው፤ ማፍረስ ቀላል ሥራ ነው፤ ጭንቅላትም፣ ማሰብም አይጠይቅም፤ ልብም፣ ስሜትም አይጠይቅም፤ የሚጠይቀው የዝሆን አካልና ጉልበት ብቻ ነው፤ አንድ ቤተሰብ ስንት ዓመት በዚያ ቤት ውስጥ ኖረ? ጎረቤቶች ምን ዓይነት ትስስር አላቸው? በማኅበር፣ በእድር፣ በዝምድና በቤተ ክርስቲያን ወይም በቤተ መስጊድ፣ በመቃብር፣ በሥራ፣ በአጠቃላይ የእያንዳንዱ ሰው ኑሮ ከልደት ጀምሮ የተፈተለበትና የተደራበት ውስብስብ የኅብረተሰብ አካል መኖሪያ ነው፤ ይህንን አካል ለማፍረስ ትንሽ ጭንቅላትና ግዙፍ ጡንቻ ያለው አይቸግረውም፡፡
መኖሪያ ቤቶችን ማፍረስ፣ መቃብሮችን ማፍረስ፣ የንግድ ድርጅቶችን ማፍረስ፣ ትምህርት ቤቶችን ማፍረስ፣ … ማፍረስ… ማፍረስ… ማፍረስ! ሳያለቅሱ እያስለቀሱ ማፍረስ፤ መሬቱን ማራቆት፣ ሰዎቹን ማራቆት፤ እያፈረሱ ማራቆት፤ እያራቆቱ ማስለቀስ፤ እያስለቀሱ ማፈናቀል፤ እያፈናቀሉ መጣል፤ የሚፈርሰው ቤት ብቻ አይደለም፤ የሚራቆተው መሬት ብቻ አይደለም፤ የሚፈርሰው ሰው ነው፤ የሚፈርሰው ከልደት ጀምሮ የነበረ ጉርብትና ነው፤ የሚፈርሰው ለዘመናት የተገነባ ዝምድና ነው፤ የሚፈርሰው የኑሮ የመደጋገፍ ተስፋ ነው፤ የሚፈርሰው የ‹‹ቀባሪ አታሳጣኝ!›› ጸሎት ነው፤ የሚፈርሰው የአጥቢያና የእድር የቀብር ዋስትና ነው፤ የሚበጣጠሰው ለብዙ ዘመናት የቆየ፣ በደስታና በሐዘን፣ በሳቅና በለቅሶ ማኅበረሰቡን ያስተሳሰረው ገመድ ነው፤ ይህ ለዘለዓለም ጠፍቶ የሚቀር፣ ማንም በምንም የማይተካው ማኅበረሰባዊ ክስረት ነው፤ የትውልድ መቋረጥ ነው፤ የታሪክ መቋረጥ ነው፤ የማይሽር የዜግነት ቁስል ነው፤ ከዜግነት የአገር ባለቤትነት ወደባይተዋርነት፣ ከሰውነት ወደኢምንትነት፣ ወደገለባነት መውረድ ነው፤ መዋረድ ነው፤ የተወለዱበትና ያደጉበት በጉልበተኞች ሲፈርስ አቅመ-ቢስ ሆኖ መፈናቀል፣ አገሬ ነው ባሉት ቦታ ባይተዋር ሆኖ መሰደድ ነው፤ በሌላ አገር ተሰድዶ ሁለተኛ ዜጋ መሆንን የሚመርጡ ሞልተዋል፤ ያውም ከተገኘ!

ወሬ ይገድላል


(ርዕሰ አንቀጽ)
new years resolutions

በጎርጎሪያኑ የቀን መቁጠሪያ ለምትገለገሉ ሁሉ መልካም አዲስ ዓመት!! በአዲሱ ዓመት ከራስ ጋር በመታረቅ፣ ከህሊናና ከእዕምሮ ባርነት በመላቀቅ፣ ከይሉንታ ጥብቆ ውስጥ በመውጣት፣አካሄድን ለማሳመር ይቻል ዘንድ የተጠቀለለውን አሮጌ ዓመት ትምህርት ማድረግ ታላቅ ጉዳይ ነው። አዲሱ ዓመት ከባከኑት ዓመታቶች ጋር ተዳምሮ እንዳያጎብጠን፣ ተስፋችንን እንዳይበላውና ወደ ከፋ የፖለቲካ መሰላቸት ውስጥ እንዳይከተን መጠንቀቅ ደግሞ ከሁሉም በላይ ወሳኝ ይመስለናልና ከከንቱና የማያንጽ ወሬው ቆጠብ፣ ከተግባሩ ጨመር እናድርግ!! ወሬ ይገድላል እንዲሉ!!
ይሉኝታን እንቅበር ባለፉት ዓመታት የይሉኝታ ፖለቲካ ጉዳት አድርሷል። በይሉኝታ በመነዳት የማይረሳ ኪሳራ ተመዝግቧል። በይሉኝታ ብቻ የደረሰብን የፖለቲካ ጠባሳ ሰምበሩ በያንዳንዳችን ሰውነት ላይ ይታያል። በተፎካካሪ ፓርቲዎችና ለለውጥ በተነሱ ፓርቲዎች ውስጥ ብዙ የሚሰሙ ጉዳዮች አሉ። በየጓሮ የሚሰማው የሃሜት፣ የጀግንነትና የአሉባልታ ትግል የሚቆመው ይሉኝታ ሲሰበርና ፊትለፊት መግጠም ሲቻል ነውና የይሉኝታን አርበኝነት እንቅበር!! ይህ የአዲስ ዓመት የመጀመሪያው የቤት ስራ ይሁን!! በተግባርም ይታይ!!

ራስን ማክበር አብዛኛውን ጊዜ ስለ ህሊናና አእምሮ ባርነት ይነገራል። ሰዎች ከዚሁ ከአእምሮ ባርነት ራሳቸውን ነጻ እንዲያደርጉ ምክር ሲሰነዘር በተደጋጋሚ ይሰማል። ምክሮቹና ትምህርቶቹ ምን ያህል ተግባራዊ እንደሆኑ ባናውቅም ባጭሩ ግን የ“ባርነት” ዋናው መሰረት ራስን አለማክበር ነውና የራሳችንን ዋጋ እንወቅ። ራሳችንን አክብረን፣ ክብራችንንና ዋጋችንን ጠብቀን፣ ስንጓዝ ከባርነት እንላቀቃለንና ለራሳችን ክብር እንስጥ። በከበርን ቁጥር ከስሜትና ከግብታዊ የፖለቲካ ትግል ራሳችንን በማረቅ አካሄዳችንን የማስተካከል እድል እናገኛለን። በእንዲህ መልኩ ስንደግፍም ሆነ ስንደገፍ አንወድቅም። በዚህ ዓይነቱ መደጋገፍ ውስጥ ተግባር እንጂ ፕሮፓጋንዳ ቦታው ያንሳል። መተማመን ይሰፍናል። ዛሬ እልል ብለን ነገ ከማዘን እንድናለን።ሁላችንም ራሳችንን ስናከብር የጋራ ራዕይና የጋራ መሪ ለመሰየም አንቸገርም። የሰየምነውንም መሪ አምኖ ለመቀበል ጊዜ አናመነዥግም። ሰባኪና ደቀ መዝሙርም አያስፈልግም። እናም ራስን ማክበር ዋጋው ታላቅ ይሆናል። ከመነዳትም ያድናልና!!