አንዷለም አራጌ ዋለ (ከቃሊቲ ማጎሪያ) ክፍል ሁለት
በሀገሬ ሰማይ ስር በሚደረገው የተቃውሞ ፖለቲካ እንቅስቃሴ ከኢዴፓ እስከ አንድነት ፓርቲ ድረስ በመሳተፍ ለአስራ ሶስት ዓመታት ያህል የምችለውን አስተዋጽኦ አድርጌያለሁ፡፡ ይህ ኩነትም የፓርቲዎችን ጓዳ ፈትሼ ግንዛቤ እንዳገኝ ስላመቻቸልኝ፣ በቀጣይ ህዝባችን የፖለቲካና ሰብአዊ መብቶቹ ተከብረው ነፃነቱን እንዳያገኝ እንቅፋት ሊሆኑ ይችላሉ ብዬ የማስባቸውን ነጥቦች እንደሚከተለው ለማቅረብ እወዳለሁ፡፡
1-እንደ ገዥው ፓርቲ፣ ተቃዋሚ ድርጅቶችም ከኋላቀሩ የፖለቲካ ባህላ የተላቀቁ አለመሆናቸው ነው፡፡ እናም አዲስ የፖለቲካ ባህል ለማስጀመር ከመስራት ይልቅ ሳያውቁት ከዘመነ-መሳፍንት የተቀዳውን የፖለቲካ ባህል በተሻለ ተግባራዊ ለማድረግ ሲንቀሳቀሱ ዛሬም ይታያሉ፡፡
2-የእስከ ዛሬውን የከሸፈ ሂደት የገመገመና የኢትዮጵያን ህዝብ ለአንዴና ለመጨረሻ ከተጫነበት የጭቆና ቀንበር ለማላቀቅ የሚያስችል በውል የታሰበበትና የተጠና የፖለቲካ ቀመር እጦት በተቀቃዋሚ ፓርቲዎች ዘንድ በጉልህ ይንፀባረቃል፡፡
3-የማያምኑበትን መቃወም ተገቢ የሆነውን ያህል የየራሳችንም ህፀፆች ያለርህራሄ ማየት፣ አይቶም ነቅሶ ማውጣት ተገቢ ነው፡፡ ነገር ግን በተቃዋሞ ጎራ ባለነው ፖለቲከኞች ላይ ይህንን የማድረግ ችግር ይታይብናል፡፡ ህፀፆችን ቀድሞ ማየቱ ከሌላ ወገን የሚሰነዘረው ነቀፋ ምክንያቱን ለመረዳት እድል ይሰጣል፡፡ በትችት ከመሰበርም ይታደጋል፡፡
4-ከ1960ዎቹ ጀምሮ የኢትዮጵያ ፓርቲዎች መለያ ከሆኑት አንዱ ‹ግትርነት› መሆኑ አከራካሪ አይመስለኝም፡፡ ይህ ሁኔታ በፓርቲዎች መካከል ብቻ ሳይሆን፣ በራስ ፓርቲ አባላት ውስጥም የሚፈጠሩ ችግሮች ከግትርነት የሚነሱ ናቸው፡፡ ‹‹መሸነፍ››፣ ‹‹ማሸነፍ››፤ ‹‹መንበርከክ››፣ ‹‹ማንበርከክ›› በሚለው የጫወታ ህግ ታስረን በቆምንበት ስንረግጥ በአስከፊው የመከራ ዘመን እንድንቆይ አድርጐናል፡፡ ችግር የመፍቻ ስልትም ሆነ ባህል አላዳበርንም፡፡ እንዲያውም የትግሉ እንቅስቃሴ ከአገዛዙ ጋር መሆኑ ቀርቶ በእኛ መካከል ሆኗል፡፡