ኮንትራቱስ ይቁም፣ የቀሩትን ዜጎች መብት ማን ያስከብር?
ሳውዲዎች ከኢትዮጵያ ከኬንያና ከኢንዶኖዥያ የቤት ሰራተኛ ቅጥር ካቆሙ ሰነባበተ! ይህነኑ ተከትሎ የቤት ሰራተኛ እጥረት የሳውዲዎች መነጋገሪያ ሆኗል። ባለጸጎቹ የሳውዲ ዜጎች በያዝነው የረመዳን ወር ብቻ 32 ቢሊዮን ሪያል የሚገመት ገንዘብ በሃገር ውስጥ ገበያ ልውውጥ ላይ እንደዋሉ በሰማን መባቻ የሳውዲዎች ችግር ሆኖ በመነገር ላይ ያለው የቤት የሰራተኛ አቅርቦቱን ጉዳይ ነው። ይህንንም የሃገሪቱ ታዋቂ መገናኛ ብዙሃን ሰፊ ሽፋን ሰጥተው በመዘገብ ላይ ናቸው ። በሰራተኛ አያያዝ በኩል አለም አቀፍ ውግዘት ተለይቷቸው የማያውቁት ሳውዲዎች እንደ ኢትዮጵያ መንግስት ተወካዮች ለዜጎቹ መብት ተከራካሪ የሌላቸውን ዜጎችን ጩኽት መስማት ተስኗቸዋል። “ስብአዊ መብት ገፈፋ ደረስብን!” ሲሉ የዝሆን ጀሮ ይስጠኝ ብለው ይስተዋላሉ ፣ ይህም የሚጠፋው ጥፋት እንደዳይታረም አድርጎታል። የአሁኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ክብር አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እያሉ ከሳውዲዎች ጋር በህግ ማዕቀፍ ሳይስማሙ መንገዱን ከከፈቱት ወዲህ ባለፉት ሶስት አመታት ከግማሽ ሚሊዮን ያላነሱ ኢትዮጵያውያን በኮንትራት ስራ ስም ወደ ሳውዲ ገብተዋል። ሳውዲዎች ከዛሬ ከሶስት አመት በኋላ በአያያዝ ጉድለት ጥፋትና ወንጀል ሲከተል ጤናቸው ተሟልቶ የተቀበሏቸውን ዜጎች በሽተኛ ላካችሁብን እስከሚል ቧልት ተሻግረዋል። ዜጎች ባለፉት አመታት ህጋዊ ተብለው እየመጡ ህገ ወጥ የመብት ገፈፋ ይፈጸምባቸዋል።
ለዚህ ሁሉ በደል ግን ሳውዲዎችን ብቻ መውቀስ ሚዛናዊ አያደርግም ባይ ነኝ! ይህን የምልበት ዋንኛ ምክንያት ከኢትዮጵያ በኩል የሚላኩት ሰራተኞች ያለ በቂ ቅድመ ዝግጅትና ህጋዊ የሁለቱ ሃገራት የኮንትራት ውል ካለመላካቸው ባሻገር ስለመጡበት ስራ ፣ ስለመጡበት ሃገር፣ አረብኛ ቀርቶ የሃገራችን ብሔራዊ ቋንቋ አማርኛ መናገር የማይችሉ ከገጠሩቱ የሃገራችን ክፍል ተግዘው የመጡ መገኘታቸውን አውቃለሁና ነው! ለ ስራ ያልደረሱ ታዳጊዎች እንደሚላኩ አይቻለሁና ነው! በዚህ መሰል መንገድ የመጡት ዜጎች የት እንደሚገቡ? የት እንደሚድርሱና ምን እንደሚፈጸምባቸው አለመታወቁ ሳውዲ ሲገቡ ክትትል ተደርጎ አይመዘገቡምና ነው! በተባራሪ የምናየው የመብት ገፈፋ በመቶ ሽዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን እንደጨው በየ ሳውዲው ገጠር ከተማ ተበትነው ሊደርስባቸው የሚችለውን አደጋና ተደራሽ አለመሆናቸውን በግልጽ ያሳይ ይመስለኛል። ይህን ስል ሰብአዊ መብታቸው ተጠብቆ በሰላም መስራት የቻሉ በሽዎች የሚቆጠሩ መኖራቸውን ጭምር በመጠቆም ነው። ስለሚደርሰው በደል ስናወራ ግን ከላይ እንዳስቀመጥኩት ለዚህ የመብት ጥሰት ዋና ተጠያቂ አሰሪዎች ቢሆኑም የኢትዮጵያ መግስት ተወካዮች ለተሰየሙበት የዜጎች መብት ጥበቃ ዋና አላማ ትግበራ ዳተኛ መሆናቸው በተጠያቂነቱ ረድፍ ያሰልፋቸዋል። ይህ ዳተኝነትም ችግሩ ከመቀነስ እንዲስፋፋ ምክንያት ሆኗል!