Thursday, August 7, 2014

የዋሽንግተኑን የአፍሪቃ መሪዎች ጉባኤ ኢትዮጵያውያን ተቃወሙት


"ኦባማ ዝምታው ይብቃ"

ethio us
ኢትዮጵያውንና ኢትዮጵያውያን አሜሪካውያን በዛሬው እለት በዋሽንግተን ዲሲ የተከፈተውንና በዩናይትድ ስቴትሱ ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ ከአፍሪቃ መሪዎች ጋር የሚያደርጉትን ጉባኤ በመቃወም አደባባይ ወጥተዋል።
“በኢትዮጵያ የሚታየው የሰብዓዊ መብት ረገጣ እንዲቆም አዎንታዊና ተጨባጭ ግፊት በማድረግ ፋንታ፤ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶቹን አራማጆች በመደገፍ ሁኔታው ይበልጥ እንዲባባስ እያደረገ ነው፤” ሲሉ ከተለያዩ የዩናይትድ ስቴትስ ግዛቶች የመጡ መሆናቸውን ያስታወቁት የሰልፉ ተሳታፊዎች የኦባማን አስተዳደር ኮንነዋል።
ስብሰባውን አስመልክቶ የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ወደ ርዕሰ-ብሔርነቱ በዘለቁ ወቅት ሃገራቸው ከነበረችበት የምጣኔ ኃብት ድቀት አሁን እያገገመች በመሆኗ ትኩረታቸውን ለአፍሪካ እየሰጡ መሆኑን የሚያሳዩ ክንዋኔዎችን እያደረጉ ነው በማለት ቀድሞ በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሣደር የነበሩትና የጆርጅ ዋሽንግተን ዩኒቨርሲቲ ረዳት ፕሮፌሰር ዴቪድ ሺን መናገራቸውን ያሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ ዘግቦ ነበር፡፡

Friday, August 1, 2014

ዘረኛው የትግሬ-ወያኔ ቡድን በሰሜን ጎንደር የዐማራ ሕዝብ ላይ የፈጸመው የዘር ማጽዳት እና የዘር ማጥፋት ወንጀል

end genocide now
የትግሬ-ወያኔ ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያዊነትን ለማጥፋት አቅዶ ሲነሳ፣ የግቡ መረማመጃ ያደረገው የኢትዮጵያዊነት መገለጫ የሆኑ ተቋሞችን፣ ኃይማኖቶችን፣ ዕሴቶችን እና በተለይም «ዐማራ» የተሰኘውን ነገድ ተወላጆች ነጥሎ ማጥፋት የሚል ሥልት በመከተል እንደሆነ ይታወቃል። በዚህም መሠረት የጥፋቱ ቅድሚያ ዒላማ ያደረገው ለትግራይ ሕዝብ በችግሩ ጊዜ ደራሽ እና የተራበ አንጀታቸውን ዳሳሽ በሆነው የወልቃይት፣ የጠገዴ፣ የጠለምትና የሠቲት ወረዳዎች ሕዝብ ላይ ነው። ወያኔ በእነዚህ የትግሬ አዋሣኝ ወረዳዎች ሕዝብ ላይ የጥፋት ክንዱን የዘረጋው በሦስት መሠረታዊ ምክንያቶች ነው።
የመጀመሪያውና ታላቁ ምክንያት የእነዚህ ወረዳዎች ሕዝብ ዐማራ በመሆኑ እና የትግራይ አዋሳኝ ስለሆነ የትግራይን ታሪክ ክፉውንም ሆነ ደጉን ጠንቅቆ የሚያውቅ በመሆኑ ነው። በዚህም ምክንያት የዚያ አካባቢ ሕዝብ የትግሬ-ወያኔ ለተነሳለት ፀረ-ኢትዮጵያ እና ፀረ-ዐማራ እንቅስቃሴ የማይተኛ እንደሆነ ስለሚረዳ ይህን ሕዝብ ብቻውን አቁሞ ማጥፋት ለወደፊቱ ግሥጋሴው ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥርላቸው በማመን የችግር ጊዜ ደራሻቸውን ሕዝብ ያለርኅራኄ ጨፍጭፈውታል።
ሁለተኛው ምክንያት «ታላቋን ትግራይ» ለመመሥረት ባላቸው ዕቅድ ለውጭ ግንኙነታቸው መውጫ መግቢያ እንዲሆናቸው ከሱዳን ጋር የሚዋሰኑትን እነዚህን ወረዳዎች ወደ ትግራይ ማጠቃለል ስለነበረባቸው ነው። ሆኖም የአካባቢው ሕዝብ «ነገዳችን ዐማራ፣ ጠቅላይ ግዛታችን ጎንደር ነው።» እያለ እንዳያስቸግራቸው በቅድሚያ ነባር ነዋሪውን ጎንደሬ አጥፍቶ በሠፋሪ ትግሬ ማስያዝ ለዓላማቸው ሥምረት ያገለግላል ብለው በማመናቸው ነው።

Friday, July 25, 2014

ፖሊሶቻችን ተዉ ቀልብ ግዙ!


Untitled-1ፖሊሶቻችን ተዉ ቀልብ ግዙ!
ይሄንን ፎቶ ልብ ብዬ እንዳየሁት፤
የሆነው ባለፈው አርብ የረመዳን ጁማዓ ጸሎት በሚደረግበት ወቅት ነበር። ሙስሊሙ ህብረተሰብ እንደተለመደው ሰላማዊ ተቃውሞውን ለማሰማት ገና ሲጀመር፤ ሌላ የፎቶ ማስረጃ እንዳሳየን ፖሊሶች ድንጋይ መወርወር ጀመሩ፤ (ይሄንን ስንናገር እየተሸማቀቅንም ቢሆን ግን እውነት ነው) በዚህም ብጥብጡ ተነሳ ፖሊሶች ያገኙትን መደብደብ ጀመሩ፤ ድብደባው እስላም ክርስቲያን ያለየ ለመሆኑ የሰማያዊ ፓርቲዋ ወይንሸት ሞላ እማኝ ነች። በእለቱ ፖሊሶች እና ደህንነቶች ያደረሱትን ስቃይ ድምጻችን ይሰማ ዎች ”ጥቁር ሽብር” ብለው ሰይመውታል።
በፎቶው ላይ የሚታዩት ሙስሊም ሰውዬም እንግዲህ ከተደብዳቢዎች አንዱ ነበሩ ማለት ነው። በዚህ ድብደባ ላይ የሚያስገርሙ ሁለት መሰረታዊ ነገሮች አሉ። አንደኛው እኒህ ሰውዬን ለመደብደብ ስምንት ፖሊሶች ከበዋቸዋል። ”አንድ ለአምስቱ አደረጃጀት ወደ አንድ ለስምንት አደገ” ብለን እንዳናሾፍ፤ እየተደደቡ ያሉት ሰብዓዊ ፍጡር ናቸው እና ለቀልድ አይመችም። ሁለተኛው እና በጣም የሚደንቀው ግን የፖሊሶቹ ፈገግታ ነው። አንዳንዶቹማ ፍንክንክ እያሉ ሲስቁ የሰርግ ጌሾ የሚወቅጡ እንጂ እንደነርሱ ሰው የሆንነ ፍጡር የሚደበድቡ አይመስሉም።
እነዚህ ፖሊሶች በአደባባይ እንዲህ ከደበደቡን በየእስር ቤቱ ጓዳማ ምን እያደረጉን እንደሆነ መገመት ይጨንቃል።
እወነቱን ለመናገር የመጨረሻው ቀን ቀርቧል። ሌላው ሁሉ ቢቀር እንዲህ እየተደበደብን ኢህአዴግን ከሚቀጥለው ምርጫ አናሳልፈውም። ኑሮ የሚደበድበን አንሶ ያልጠገቡ የመንግ ፖሊሶች ደግሞ እየደበደቡን መኖርን የምንመርጥ እኛ ማን ነን…
ፖሊሶቻችን ተዉ… ሞልቶ ለማይሞላ አዱኛ፤ ቀለባችሁን ብቻ አትመልከቱ ቀልብም ለመግዛት ሞክሩ።

Friday, July 18, 2014

በኢትዮጵያ የእንግሊዝ እርዳታ ፖሊሲ ተግባራዊነት እንዲፈተሽ ታዘዘ


dfid
የእንግሊዝ የባሕር ማዶ ትብብር ኤጀንሲ ለኢትዮጵያ ድጋፍ ሲሰጥ ከራሱ የሰብዓዊ መብቶች ፖሊሲዎች ጋር በተጣጣመ መልክ መሆንና አለመሆኑ እንዲፈተሽ አንድ የእንግሊዝ ፍርድ ቤት መወሰኑን የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቹ ሂዩማን ራይትስ ዋች አድንቋል፡፡
ሌስሊ ሌፍኮው - የሂዩማን ራይትስ ዋች የአፍሪካ መርኃግብር ምክትል ዳይሬክተር
ሌስሊ ሌፍኮው – የሂዩማን ራይትስ ዋች የአፍሪካ መርኃግብር ምክትል ዳይሬክተር
የእንግሊዝ የባሕር ማዶ ትብብር ኤጀንሲ ለኢትዮጵያ ድጋፍ ሲሰጥ ከራሱ የሰብዓዊ መብቶች ፖሊሲዎች ጋር በተጣጣመ መልክ መሆንና አለመሆኑ እንዲፈተሽ አንድ የእንግሊዝ ፍርድ ቤት መወሰኑን የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቹ ሂዩማን ራይትስ ዋች አድንቋል፡፡
የእንግሊዝ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ትናንት፤ ሐምሌ 7/2006 ዓ.ም ባሣለፈው ውሣኔ የዓለም አቀፍ ትብብር መሥሪያ ቤቱ ለኢትዮጵያ ድጋፍ ሲሰጥ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶችን የሚያሳዩ ማስረጃዎችን በበቂ ሁኔታ አይፈትሽም ሲባል የቀረበበት ክሥ ሙሉ የፍርድ ቤት ምርመራ የሚያስፈልገው ነው ብሏል፡፡
የሂዩማን ራይትስ ዋች የአፍሪካ መርኃግብር ምክትል ዳይሬክተር ሌስሊ ሌፍኮው ለዝግጅት ክፍላችን በሰጡት ቃል ይህ የእንግሊዝ ፍርድ ቤት ውሣኔ ገና የመጀመሪያ እርምጃና ሊደነቅ የሚገባው ነው ብለዋል፡፡
በጋምቤላ፣ በሶማሌ ክልልና በደቡብ ኦሞ እየተፈፀሙ ናቸው ያሏቸው አድራጎቶችም የቅርብ ፍተሻ የሚያስፈልጋቸው መሆናቸውን የጠቆሙት ሚስ ሌፍኮው ልማት ከሰብዓዊ መብቶች መከበር ጋር አብሮ መታየት እንደሚገባቸው ለጋሾች ሊገነዘቡ ይገባል ብለዋል ሚስ ሌፍኮው፡፡
መሠረታዊ የልማት ድጋፍ ይቁም የሚል አቋም ሂዩማን ራይትስ ዋች እንደሌለው ሌፍኮው አመልክተው የእንግሊዝ መንግሥት ለኢትዮጵያ በሚሰጠው እርዳታ ሰብዓዊ መብቶችን የሚረግጡ ፕሮጀክቶችን የሚያስፈፅሙ ባለሥልጣናት ደመወዝ እንደሚከፈል አመልክተዋል፡፡

የማይጮኹት . . . በዓሉ ግርማን የበሉት ጅቦች


heyans vs lion
ይህችን ውድ የሆነች ትንሽ ቁራሽ ሕይወት እንደ አብርሃም ቤት የለኝ፣ እንደ ሙሴ መቃብሬ ላይታወቅ፡፡ መኖር – መጻፍ – ሕይወትን በተስፋ ወደፊት እየኖርኩና ወደኋላም እያስተዋልኳት፡፡” በዓሉ ግርማ – ደራሲው
1እውቁን ጋዜጠኛና ደራሲ በዓሉ ግርማን በአጸደ ሕይወት ካጣነው፤ በዘንድሮው የካቲት 24 ቀን 2006 ዓ.ም. ሠላሳ ዓመታት  ተቆጥረዋል፡፡ ውድ ባለቤቱ ወይዘሮ አልማዝ አበራ በዘመነ ኢሕአዴግ ስለ ባለቤቷ ከቤት እንደወጣ መቅረት ጉዳይ ከፍተኛው ፍርድ ቤት ቀርባ የጠቅላይ አቃቤ ሕግ ምስክርነቷን እንድትሰጥ ተደርጋ ነበር፡፡ ያንን የእሷን የፍርድ ቤት የምስክርነት ቃል የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን አቅርቦ ካስደመጠንም ሁለት አሠርታት ዓመታት እንደዋዛ ሊቆጠሩ ነው፡፡ ውድ ባለቤቱ ወ/ሮ አልማዝ ለከፍተኛው ፍርድ ቤት  ያቀረበችውና እልክና ቁጭት የተመላበት የምስክርነት ቃሏ አንድምታ እንዲህ የሚል ነበር፡፡
“. . . የካቲት 24 ቀን 1976 ዓ.ም. ቀን ላይ አስፋው ዳምጤ እቤት ስልክ ደወለ፡፡ በዓሉ ቤት አልነበረምና ስልኩን አነስቼ ያነጋገርኩት እኔ ነበርኩ፡፡ የእግዜር ሰላምታ ከተለዋወጥን በኋላ ‘. . . በዓሉ እንደመጣ እዚያ እቀጠሯችን ቦታ ባስቸኳይ እንድትመጣ ብሎሃል በዪልኝ . . . ’ ብሎ ስልኩን ዘጋ፡፡ በዓሉ ወደ አሥራ አንድ ሰዓት ገደማ ወደ ቤት ሲመጣ መልእክቱን ነገርኩት፡፡ ወዲያው ሻወር ወስዶ ወጣና ለመሄድ ሲጣደፍ፣ ’እደጅ ውለህ መምጣትህ ነውና እባክህ ትንሽ እህል ብጤ ቀምሰህ ውጣ’ ብለው፤ ‘አልችልም. . . ብርቱ ቀጠሮ አለንና ወደዚያው መፍጥን አለብኝ’ ብሎኝ ፈጥኖ ከቤት ወጣ፡፡  የማታ ማታ ወደቤት ይመለሳል ብዬ እስከ እኩለ ሌሊት ድረስ ብጠብቅም የውሃ ሽታ እንደሆነ ቀረ፡፡ ቢቸግረኝ አስፋው ቤት ደወልኩ፡፡ ሚስቱ ስልኩን አነሳች፡፡ ‘. . . አስፋው እቤት ገብቷል?. . .’ ስል ጠየቅኋት፡፡ ‘. . . አዎን ገብቷል. . .’ አለችኝ፡፡ ይሄኔ ግራ በመጋባት፤ ‘. . . ባሌን ከቤት ጠርቶ ወስዶት የት ጥሎት ነው እሱ ተቤቱ የገባው?. . .’ እያልኩ አፋጠጥኳት፡፡ ቀጥዬም ‘እስኪ አቅርቢልኝና ላናግረው. . .’ ስላት፤ ‘የገባ መስሎኝ ነበር እንጂ አልገባም’ ብላ የመጀመሪያ ቃልዋን አጠፈችብኝ፡፡ የስልክ ንግግራችንም በዚሁ ተቋጨ፡፡ ሌሊቱንም እሱን ያየ እያልኩ በየቦታው እየደወልኩ ብጠይቅም፤ አየነው የሚል ሰው ሳላገኝ ነጋልኝ. . . አሁንም ለክቡር ፍርድ ቤቱ አቤት የምለው፤ አስፋው ዳምጤ ባለቤቴን በዓሉ ግርማን ከቤት ጠርቶ ወስዶ የት እንዳደረሰው ቀርቦ እንዲጠየቅልኝ ነው. . .” ስትል ነበር – ለከፍተኛው ፍርድ ቤት ምጻኔዋን ያቀረበችው፡፡ ወ/ሮ አልማዝ ይህንኑ ካስፋው ዳምጤ ጋር የተያያዘ ጉዳይ፣ ለዚህ ጽሑፍ አቅራቢና ባሁኑ ጊዜ ተቀማጭነቱ ባሜሪካን አገር ለሆነ አንድ ሌላ ጋዜጠኛ ልንጠይቃት ወደ መኖሪያ ቤታቸው በሄድን ጊዜ ይህንኑ ሁኔታ ዘርዝራ አጫውታን እንደነበር ያስታውሳል፡፡

Sunday, July 13, 2014

ጥላቻ በዛ፣ ቂም አበበ፣ በቀል አፈራ!! ኢህአዴግም አልረካም


የአንዳርጋቸው ጽጌ ጉዞ አስቀድሞ እንዴት ታወቀ?

prisoners1
“እነሱ ሁለት አገር አላቸው። ኢትዮጵያን ይዘዋታል። በስደትም እንደፈለጋቸው እየኖሩ ነው። እኛ ግን አንድም አገር የለንም። በስደት እንኳን እንዳንኖር እየተደረግን ነው። ሸሽተን በተሰደድንበት ምድር እንኳን ዋስትና የለንም። ከዚህ በላይ ምን ይምጣ?” ይህንን የዛሬ ሶስት ወር ገደማ ለጎልጉል የተናገሩት በኖርዌይ የኢትዮጵያ ስደተኞች ማህበር ጸሐፊ ወ/ት የሺሃረግ በቀለ ነበሩ። የወ/ት የሺሃረግን ሃሳብ በመንተራስ ለጎልጉል አስተያየት የሰጡ እንዳሉት “አገር ውስጥም እስር፣ በስድት ምድርም ስጋትና እስር ካለ፣ የይለይለት መንፈስ መነሳቱ አይቀርም። ሰዎች የመኖር ተስፋቸው ሲመናመን የፈለገው ይምጣ ይላሉ። አሁን ኢህአዴግ ከስጋቱ ብዛት እየፈጸመ ያለው ድርጊት ሰዉን ሁሉ ወደዚሁ የሚያመራ ነው።”
ሰሞኑን ኢህአዴግ የወሰደውን፣ ቀደም ሲልም በተመሳሳይ ሲከናውን የቆየውን፣ ወደፊትም በቀጣይነት የሚገፋበትን እስርና አፈና አስመልክቶ የተፈጠረው ስሜት ከራር ነው። ኢህአዴግ ቋንቋው ሁሉ እስር መሆኑ እየፈጠረ ያለው ስሜት ኬላና ልጓሙ እንዳይፈርስ የሚሰጉ ጥቂት አይደሉም። የኢህአዴግ የአፈና መረብ ያልገባበት ቤትና መንድር እንዲሁም ክልል የለም። በሃይማኖት ቤትም ያለው እሳትና ችግር ቀን የሚጠብቅ ነው። ኢህአዴግ ግን ሁኔታዎችን ከመመርመር ይልቅ ቋንቋውና መፍትሄው እስርና አፈና ብቻ መሆኑ አስገራሚ እንደሆነ ስምምነት አለ።
የሰሞኑ አጀንዳ
“የጦር አውሮፕላን በመያዝ ኢህአዴግን ያመለጡ ወገኖች የመን አመቺ ብትሆንም እንደማይመርጧት ይናገራሉ። የመን ከቶውንም የማይታመን አገር እንደሆነ ሰፊ ግንዛቤ አለ። አቶ አንዳርጋቸው ታዲያ እንዴት ሰንአን ረገጡ? ምን ቀን ጣላቸው? እሳቸው በየመን ትራንዚት እንደሚያደርጉ አስቀድሞ መረጃው እንዴት ደረሰ? ከሦስት ሳምንት በፊት ስለሚያደርጉት በረራ ማን? እንዴት? መረጃ አስተላለፈ? የሚሉት ጉዳዮች በዋናነት መመርመር ግድ ነው። ቀጣዩ የቤት ስራም ይህ ነው።” ይህ በኢሜል ከደረሰን በፖሊሲያችን መሰረት ከማናትመው ሰፊ ጽሁፍ የተቀነጨበ ነው። ጽሁፉ ሌሎች የበረራ አማራጮች ስለመኖራቸውም ያወሳል። አቶ አንዳርጋቸው በተያዙበት ቅጽበት ወደ አዲስ አበባ መላካቸውና በበነጋታው ሽያጩ በትዕዛዝ ይፋ የሆነው የኢትዮጵያ ትምባሆ ሞኖፖል የትራንስ ኢትዮጵያ ሸሪክ ድርጅት ስለመሆኑም ይጠቅሳል።

Saturday, June 14, 2014

የኢትዮ-ኤርትራ የድንበር ጉዳይ ለምን አይቋጭም?


"የለዘብተኞችና የእስስት” ፖለቲካ ልዩነት እየፈጠረ ነው

ethio er
መለስ በሁለቱ አገሮች ድንበር ላይ “የጅራፍ ድምጽ እንኳን አይሰማም” በማለት ሲመጻደቁበት የነበረው የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት በ”ወረራ” እና “ወረራን መቀልበስ” በሚል ድራማ ተጀምሮ ከተቋጨ አስራ አምስት ዓመት አልፎታል። ኢህአዴግና ሻዕቢያ ጉዳያቸውን በጠረጴዛ ዙሪያ ወይም በጡንቻ መቋጨት ያልቻሉበት ምክንያት ለብዙዎች እንቆቅልሽ ሆኖ እስካሁን አለ። ሁለቱም ወገኖች ድንበር ላይ ወታደር አፍስሰው መቀመጣቸውን አስመልከቶ “አውቀው ነው” ከሚለው ውሃ የማይቋጥርአስተያየት ጀምሮ በርካታ ጉዳዮች በገሃድና በሹክሹክታ ሲሰማ ቆይቷል።
ጎልጉል የዜና ምንጮች ሰሞኑን ከአዲስ አበባ የላኩት መረጃ ግን በይዘቱ የተለየ ነው። ይህንኑ አዲስ ጉዳይ የሚመለከታቸው ክፍሎች አስተያት እንዲሰጡበት ያደረግነው ሙከራ ባይሳካም ዜናው ለውይይት የሚጋብዝ በመሆኑ አትመነዋል
የድንበር ውዝግቡ አንዲቋጭ ይፈለጋል?
የኢትዮ-ኤርትራ የድንበር ውዝግብ ጦርነት ከኢትዮጵያ ወገን ብቻ ከ100 ሺህ በላይ ጉዳዩ በውል ያልገባቸው ወገኖች ህይወት የተገበረበት ነው። የአይደር ትምህርት ቤት ህጻናትን ጨምሮ የበርካታ ሰላማዊ ዜጎችንና ህጻናትን ህይወትም ቀጥፎ አልፏል። አቶ መለስ ለዚህ ሁሉ ቀውስ ተጠያቂ ቢሆኑም በድንገት ተስፈንጥረው ፍርድ ቤት ህግ ሳይጠቀስባቸው አልፈዋል። “ታላቁ መሪ” በህይወት እያሉ በኤርትራ ጉዳይ በተፈጠረ አለመግባባት ትግራይ ውስጥ እስከመታገት ቢደርሱም ከጥንቃቄ ጉድለት በአንጋቾቻቸው ፈጥኖ ደራሽነት ተርፈው ተቃዋሚዎቻቸውን “ውህዳን” በማለት በየተራ አራግፈው ብቻቸውን “ውርስና ቅርስ” ለመሆን በቅተዋል።
ayider
አይደር
ከህንፍሽፍሽ፣ የልዩነት ጊዜ ጀምሮ አደባባይ የወጣው የልዩነት መሰረት በወቅቱ ይፋ ሲደርግ ኢትዮጵያውያንን አሳዝኖና አስቆጥቶ እንደነበር በወቅቱ በስፋት የተዘገበበት ጉዳይ ነው። ዛሬም ይህ ወቅት ዳግም እየተመለሰ እንደሆነ እየተሰማ ነው። “የኤርትራን ጉዳይ እንቋጭ” የሚሉ የከረረ አቋም ያላቸው ተነስተዋል። እነዚህ ወገኖች ሁለት አማራጭ በማቅረብ ሃሳባቸው ተግባራዊ ሊሆን እንደሚችል እየወተወቱ ነው።
የመጀመሪያው አሁን ያለው የመከላከያ አቅም የድንበሩን ውዝግብ በሃይል ለመቋጨት አቅም እንዳለው እየታመነ ለምን “ቸልተኛነት ተመረጠ” በሚል በቂ ጡንቻ ስለመገንባቱ አበክረው የሚከራከሩበት አግባብ ነው። ሁለተኛው ደግሞ “የኤርትራን ተቃዋሚዎች አደራጅተናል፤ ለምን እነሱ ወደ ኦፕሬሽን አይገቡም” የሚል እንደሆነ መረጃዎቻችን ያስረዳሉ።
ቸልተኞቹ ምን ይላሉ?
በዚህ ጉዳይ ቸልተኛ የሚባሉት የተለየ ምክንያት ያላቸው፣ ነገር ግን “ጦርነት አያዋጣም” በሚል በገሃድ የሚከራከሩ ወገኖች ናቸው። እነዚህ ውስን የብአዴንና የህወሃት ቁልፍ ሰዎች በትግራይ ድንበር አካባቢ አስተዳደር የሚሰሩትን ጨምሮ የኤርትራ ደም አላቸው። በደህንነትና በጸጥታ ክፍሉ አጠቃላይ መዋቀር ላይ ቁልፍ ቦታ ተጎናጽፈዋል። የመረጃ ምንጮቹ ማብራሪያ እንደሚያመለክተው እነዚህ ወገኖች “ኢሳያስን የክፉ ቀን መጠባበቂያ” ነው የሚሏቸው። ሰዎቹ ኢህአዴግ ላይ አንዳችም አይነት ስጋት እንደማይሆኑ የሚታወቅ ሲሆን ዋና ዓላማቸው “ከመሃል አገር ወይም ከመካከል ለውጥ ካልተነሳ አርፈህ ተቀመጥ” የሚል ዓይነት መንገድ የሚከተሉ ናቸው።