የእንግሊዝ የባሕር ማዶ ትብብር ኤጀንሲ ለኢትዮጵያ ድጋፍ ሲሰጥ ከራሱ የሰብዓዊ መብቶች ፖሊሲዎች ጋር በተጣጣመ መልክ መሆንና አለመሆኑ እንዲፈተሽ አንድ የእንግሊዝ ፍርድ ቤት መወሰኑን የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቹ ሂዩማን ራይትስ ዋች አድንቋል፡፡
ሌስሊ ሌፍኮው – የሂዩማን ራይትስ ዋች የአፍሪካ መርኃግብር ምክትል ዳይሬክተር
የእንግሊዝ የባሕር ማዶ ትብብር ኤጀንሲ ለኢትዮጵያ ድጋፍ ሲሰጥ ከራሱ የሰብዓዊ መብቶች ፖሊሲዎች ጋር በተጣጣመ መልክ መሆንና አለመሆኑ እንዲፈተሽ አንድ የእንግሊዝ ፍርድ ቤት መወሰኑን የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቹ ሂዩማን ራይትስ ዋች አድንቋል፡፡
የእንግሊዝ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ትናንት፤ ሐምሌ 7/2006 ዓ.ም ባሣለፈው ውሣኔ የዓለም አቀፍ ትብብር መሥሪያ ቤቱ ለኢትዮጵያ ድጋፍ ሲሰጥ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶችን የሚያሳዩ ማስረጃዎችን በበቂ ሁኔታ አይፈትሽም ሲባል የቀረበበት ክሥ ሙሉ የፍርድ ቤት ምርመራ የሚያስፈልገው ነው ብሏል፡፡
የሂዩማን ራይትስ ዋች የአፍሪካ መርኃግብር ምክትል ዳይሬክተር ሌስሊ ሌፍኮው ለዝግጅት ክፍላችን በሰጡት ቃል ይህ የእንግሊዝ ፍርድ ቤት ውሣኔ ገና የመጀመሪያ እርምጃና ሊደነቅ የሚገባው ነው ብለዋል፡፡
በጋምቤላ፣ በሶማሌ ክልልና በደቡብ ኦሞ እየተፈፀሙ ናቸው ያሏቸው አድራጎቶችም የቅርብ ፍተሻ የሚያስፈልጋቸው መሆናቸውን የጠቆሙት ሚስ ሌፍኮው ልማት ከሰብዓዊ መብቶች መከበር ጋር አብሮ መታየት እንደሚገባቸው ለጋሾች ሊገነዘቡ ይገባል ብለዋል ሚስ ሌፍኮው፡፡
መሠረታዊ የልማት ድጋፍ ይቁም የሚል አቋም ሂዩማን ራይትስ ዋች እንደሌለው ሌፍኮው አመልክተው የእንግሊዝ መንግሥት ለኢትዮጵያ በሚሰጠው እርዳታ ሰብዓዊ መብቶችን የሚረግጡ ፕሮጀክቶችን የሚያስፈፅሙ ባለሥልጣናት ደመወዝ እንደሚከፈል አመልክተዋል፡፡