June 13, 2013
አቤ ቶኪቻው
ጉዳዩ፤ በጣም አበዛኸው…!
ይቺ ለአባይ የተፃፈች ደብዳቤ ናት፡፡ አፃፃፏ “ስዲ ወ ግጥሚ” አይነት ናት፡፡ ትንፋሽ ያለው ሰው እንደ ግጥም ቢወርዳት ግጥም ግጥም ትመስላለች፡፡ ትንፋሽ የሌለው ሰው ደግሞ እንዲሁ ቢዘልቃት ስድ ንባብ ትሆናለች፡፡ እስቲ እንደዚህ አዳዲስ ፈጣራዎችን እናስተዋውቅ… ብዬ አካብጄ በአዲስ መስመር እጀምራታለሁ ትድላችሁ…!!
ውድ አባይ፤ ከእናታችን ማህጸን ተገኝተህ ገና በቅጡ ሳትጠና እና ሳትጠናና በልጅነት አፍላ ፍቅር ድንገት አየተሃት ከወደድካት ግብጽ ጋር ከተጋባህባት ዕለት አንስቶ ለጤናህ እንደምን አለህ… ከቶ!
እኛስ እንዳለን አለነው፡፡ አንተን ያኽል ወንድም፤ አንተን ያኽል አጋር፤ ውጪ ሀገር የሚኖር ታላቅ፣ እጅግ ታላቅ፣ ሃብታም የናጠጠ፤ ጥሩ ስርፋ ደህና ቦታ ይዞ የተቆናጠጠ፤ ዘመድ ቢኖረንም ዛሬም አልጠገብንም፡፡ ዛሬም አልወዛንም፡፡ ዛሬም አልወፈርንም፡፡ እንዲሁ እንደቀጠን፣ እንዲሁ እንደራበን፣ አመድ እንደመሰልን አለን አባይ፡፡ እንዲሁ አለን፡፡