Tuesday, February 25, 2014

ቦይንግ 767 – እገታ እና እንድምታው


(ክንፉ አሰፋ)

Hailemedehin-Abera
አንድ የኢህአዴግ ካድሬ፣ ቤት ለመከራየት ወደ አንዲት ወይዘሮ መኖርያ ይሄዳል። ስፍራው እንደደረሰ ሌላ ተከራይም ከወይዘሮዋ ቤት ብቅ እንዳለ አስተዋለ። ሌላኛው ተከራይ ሰይጣን ነበር። ሁለቱ ተከራዮች ሰርቪስ ቤቱን ለመያዝ እንደ ጨረታ ብጤ ጀመሩ። ሰይጣኑ 400 ሲጠራ፣ ካድሬው ግን 500 ሊሰጥ ተስማማ። በመጨረሻ፣ ወይዘሮዋ ቤቱን ለሰይጣኑ በትንሽ ዋጋ ማከራየቱን መረጡ። የወይዘሮዋ ውሳኔ እንግዳ ነገር ነበር።  ለሰይጣን፣ ለዚያውም በትንሽ ዋጋ ቤታቸውን ለመስጠት የወሰኑበትን ምክንያት ሲጠየቁ፤ “ሰይጣኑ አልወጣ እንኳን ቢል በጸበል ይለቃል። ካድሬው ገብቶ ቤቴን አልለቅም ቢለኝ ምን ላደርግ ነው?” ነበር ያሉት ወይዘሮዋ። ከፍ ባለ ገንዘብ ለኢህአዴጉ ሰርቪስ ቤታቸውን ቢያከራዩት ኖሮ ባጭር ጊዜ ዋናውን ቤታቸውን ለቀው የመውጣት ክፉ እድል ይገጥማቸው ነበር።
ዶ/ር መረራ ጉዲና ባለፈው ሳምንት ዘ ሄግ ላይ ስለ ወቅታዊ የኢትዮጵያ ሁኔታ ሲነግሩን ጣል ያደረጓት ቀልድ ናት። የዚህች ቀልድ የፖለቲካ እንድምታ ቀላል አይደለም። መልእክትዋ ሲጠቃለል የኢትዮጵያን ህዝብ እየለቀቀ መሆኑን ትነግረናለች። እየከፋ የመጣው የኑሮውና የፖለቲካ ሁኔታ የህዝቡን አእምሮ ብቻ አይደለም እየነካው ያለው። ህዝቡ እየተገፋ ሃገርሩን ለቆ እንዲሰደድ እየተገደደም ይገኛል። በተለይ ደግሞ ሃገሪቱ በድህነት ያስተማረቻቸው ምሁሮችዋንና ባለሞያዎችዋን እንደዋዛ እያጣች ከመጣች እነሆ ሁለት አስርተ-ዓመታት ተቆጠሩ።
እለተ ሰኞ የካቲት 10፣ 2006 ዓ.ም.።
የአለም ዜና ርዕስ ሁሉ ትኩረት የጣለው በኢትዮጵያዊው ፓይለት ጉዳይ ላይ ነበር። እንደዚህ አይነት ክስተት ሲፈጸም አዲስ አይደለም። ግን ይኽኛው ልዩ ነው። ይዘቱ ለየት ይበል እንጂ  በ1998 (እ.ኤ.አ.) ዩዋን ቢን በተባለ ቻይናዊ ፓይለት ከተፈጸመው ድርጊት ጋር ይመሳሰላል። የ30 አመቱ ወጣት የበረራ ቁጥር CA905 የሆነውን የቻይና አውሮፕላን በመያዝ የታይላንድን የአየር ጠረፍ ሰብሮ ገባ። የ27 አመት እድሜ ያላት ሚስቱን ይዞ ታይዋን ላይ ያረፈው ፓይለት ለዚያ አደገኛ ውሳኔ የሰጠው ምክንያት የኢኮኖሚ ችግር ነበር። የደረጃ እድገት፣ የደሞዝ ጭማሪ፣ የመሳሰሉ ከራስ ወዳድነት ያላለፉ ጥያቄዎች በማንሳት የፓይለቱ የራሱን ክብር ዝቅ አደረገው።

Thursday, February 20, 2014

የሌላቸው ባለቤቶች (ከበድሉ ዋቅጅራ ሳላስፈቅድ የተዋስሁት)


ፕ/ር መስፍን ወልደ ማርያም

have and not
በድሉ ዋቅጅራ ‹የሌላቸው ባለቤቶች› የሚል ቅራኔ ውስጥ የገባው ከተጨባጭ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሁኔታ ተነሥቶ ነው፤ አንዳንዴ ሁኔታዎች እያስገደዱን ቅራኔዎችን እንቀበላለን፤ አንድ ጌታ አሽከራቸውን ይጠሩና ባላገር ወደሚኖሩ እናታቸው ዘንድ ይልኩታል፤ ነገር ግን ‹ሞተው ከሆነ እንዳትነግረኝ› ብለው አስጠንቅቀውት ይሄዳል፤ ሴትዮዋ ሞተው ይደርሳል፤ ምን እንደሚያደርግ ግራ ገባው፤ ሲያንሰላስል ብዙ ቀናት ከቆየ በኋላ ጎፈሬውን ለሁለት ከፍሎ ግማሹን ይላጭና ግማሹን ብን አድርጎ ያበጥርና ጌታው ዘንድ ይቀርባል፤ አንዴ ጎፈሬውን እየነካካ፣ አንዴ የተላጨውን እየዳበሰ ጥያቄዎቻቸውን ሲመልስ፣ ጌታው ተቆጡና ‹ምንድን ነው የምታድበሰብሰው አርፈው እንደሁ በወጉ አትነግረኝም!› ብለው ሲጮሁበት ‹አዬ ጌታዬ አርስዎ መቼ በወጉ ላኩኝና!› ብሎ መለሰላቸው።
የበድሉ ‹የሌላቸው› በግማሽ እንደተላጨው ጸጉር ነው፤ ‹ባለቤቶች› ደግሞ እንደግማሽ ጎፈሬው ነው፤ የሌላቸው አላቸው፤ የአላቸው የላቸውም፤ እንደዚህ ያለውን ጉደኛ ሁኔታ እዚያው ጉደኛ ሁኔታ ውስጥ ካለው በቀር ሌላ ሰው አይገባውም፤ መብት ከግዴታ ሲገነጠል መብትም ግዴታም ባሕርያቸውን ለውጠው ሌላ ነገር ይሆናሉ፤ መብትም መሸጦ፣ ግዴታም መሸጦ ሲሆን ከራሱ በቀር ማን ለማን፣ ማን ለምን ኃላፊነት አለበት? መሬቱ ለሙስና ለምለም የሚሆነው እንዲህ እየሆነ ነው፤ ትንሽ መንደር ለትልቅ አገር መመሪያ ሲያወጣና የማንነት ምንጭ ሲሆን ‹‹ኢትዮጵያዊ ዝበሃል መንነት የለን፤›› ብሎ በአደባባይ መናገር ይቻላል፤ ኢትዮጵያ ውስጥ ሆኖ ኢትዮጵያዊ በሚባል ጋዜጣ ላይ ሀሳቡን እየጻፈ፣ ኢትዮጵያዊ የሚባል ብር እየተቀበለ (በጎን ሊሬም፣ ዶላርም ሊኖር ይችላል፤) ኢትዮጵያዊ የሚባል ምግብ (ማካሮኒም ሊሆን ይችላል) እየበላ፣ ኢትዮጵያ ከምትባል አገር የሚያገኘውን ጥቅም ሁሉ እያግበሰበሰ ‹‹ኢትዮጵያዊ ዝበሃል መንነት የለን፤›› ማለት ይችላል፤ ሀሳቡን የመግለጽ ነጻነት አለው፤ ግን ‹ኢትዮጵያዊ የሚባል ማንነት የለም› ብሎ የሚናገረው ለማን ነው? ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው፤ ለኤርትራውያን ነው? ለኢትዮጵያ ወጣቶች ነው? አንዱ የክህደት ትምህርቱ የገባው ወጣት ኢትዮጵያዊነት ዜግነት እንጂ ማንነት አይደለም ብሎ ጻፈልኝ፤ ፊደልን ተምረው ማንበብና መጻፍ ሲጀምሩ ድንቁርናን የሚያነግሡ ሰዎች በተፈጥሮ ያገኙትን ደመ-ነፍሳቸውን እውቀት ያደርጉታል፤ ፊደሉ የእውቀትን በር መክፈቻ መሆኑ ሳይገባቸው ይቀርና ፊደሉን የእውቀት መጨረሻ ያደርጉታል።
‹‹ኢትዮጵያዊ ዝበሃል መንነት የለን፤›› ማለት ኢትዮጵያ ባለቤት የላትም ማለት አይደለም? ይህንን የሚለው ከሌላቸው ‹‹ባለቤቶች›› አንዱ መሆኑ አይደለም? ባለቤቶች ነን የሚሉትንስ ወደባዶነት መለወጥ አይደለም (ሁሉም ዜሮ)? ባለቤት ለመሆን መጀመሪያ ቤቱ ባዶ መሆኑን ማረጋገጥ አስፈላጊ አይደለም? ኢጣልያኑ ቅኝ ገዢ አቶ ሐዲስ ዓለማየሁን ሲያይ ለዓይኑ አልሞላ አሉትና ‹‹ለካ ቤት ባዶ ሲሆን ቁንጫ ያፈራል የሚባለው እውነት ነው!›› አላቸው፤ ሌላው ቢቀር ኢጣልያኑ የተረተው በአማርኛ ነው!
‹‹ኢትዮጵያዊ የሚባል ማንነት የለም፤›› ያለው ሰው ዓላማ አለው፤ ዓላማው ኢትዮጵያን በቁንጫ መሙላት ነው፤ ኢትዮጵያዊ ማንነት ሁሉ ወደቁንጫነት ሲለወጥ እሱ አንድ ቆርቆሮ ፍሊት ይዞ የቁንጫዎች የበላይ ይሆናል፤ ይህንን የሂትለርና የናዚን ፍልስፍና የሚያረጋግጥ ሌላም ነገር አለ፤ ‹‹ትግራዋይነት ዝበሃል ንጹሕ መንነት አለና፤››! ‹‹ትግራዋይነት የሚባል ንጹሕ ማንነት አለን፤›› ማለት ነው፤ ዘረኛነትና ድንቁርና የማይለያዩ መሆናቸውን ማረጋጋጫ ነው፤ እንኳን የትግራይን ሕዝብና ራሱንም አጥርቶ የማያውቅ ሰው ስለ‹‹ንጹሕ›› ማንነት ያወራል፤ እስቲ ‹‹ንጹሕ›› ትግራዋይ የሆኑ ሰዎችን ስም ዘርዝር ቢባል እነማንን አንደሚጠራ አላውቅም፤ የጀርመን ናዚዎች ስለንጹህ የአርያን ዘር የጻፉትን በጥራዝ-ነጠቅነት በዓይኑ ዳብሶት ይሆናል፡፡

Wednesday, February 19, 2014

ዓለም ባንክ ኢህአዴግን በረበረው – ከዚያስ?


“ኢህአዴግ የተጭበረበረ ሪፖርት አቅርቦ” ነበር

world bank foto
ኢህአዴግ “አልመረመርም፣ አልበረበርም” በማለት ሲያንገራግር ከቆየ በኋላ በዓለም ባንክ ቀጭን ትዕዛዝ ለመበርበር መስማማቱን ገልጾ በተለያዩ አካላት ምርመራ ተካሂዶበታል። በተከታታይ ሲካሄድ የነበረው ምርመራ አካል የሆነው የመጨረሻ ምርመራ ባለፈው ሳምንት አጋማሽ ተጠናቋል። የጎልጉል ታማኝ ምንጮች እንደተናገሩት ስድስት አባላትን ያካተተው የዓለም ባንክ የምርመራ ቡድን ኢህአዴግን መርምሮ ተመልሷል። የሚጠበቀው የመጨረሻው ሪፖርትና ሪፖርቱ የሚቀርብለት የዓለም ባንክ የዳይሬክተሮች ቦርድ ውሳኔ ነው። በቅርቡ የሚወጣውን ውሳኔ አቅጣጫ ለማስቀየር በማሰብ ኢህአዴግ ለመርማሪው ቡድን ራሱ የፈጠረውን “የተጭበረበረ ሪፖርት” አቅርቦ ነበር፡፡
ኢህአዴግ ምርመራውን በተቀነባበረ የፈጠራ ሪፖርት ለማምለጥ ሞክሮ እንደነበር የጠቆሙት የመረጃው ምንጮች “የመርማሪዎቹ ቡድን ሪፖርቱን አንቀበልም፣ የችግሩ ሰለባዎችና ክሱን የመሰረቱት ክፍሎች በሚኖሩበት ቦታ በመገኘት ነዋሪዎችን በተናጠል ለማነጋገር እንፈልጋለን” በማለት ኢህአዴግን እንደሞገቱት አስታውቀዋል። ኢህአዴግ በልማትና በህዝብ ስም የሚያገኘውን ከፍተኛ የዕርዳታ ገንዘብ የጦር ሃይሉን ለማደራጀት፣ የደህንነትና የፖሊስ ሃይሉን ለማስታጠቅና ርዳታ በሚለመንባቸው ዜጎች ላይ የተለያየ ወንጀል ፈጽሟል፣ አሁንም እየፈጸመ ነው በሚል መወንጀሉ ይታወሳል።
የምርመራው መነሻ ከዛሬ አስር ዓመት በፊት በቀድሞው ጠ/ሚኒስትርና የጦር ሃይሎች ዋና አዛዥ፣ የህወሃትና የኢህአዴግ ሊቀመንበር አቶ መለስ ዜናዊ ቀጥተኛ ትዕዛዝና በየደረጃው ያሉ አስፈጻሚዎች በጋምቤላ ክልል የተከናወነው የጅምላ ጭፋጨፋ ነው። በወቅቱ የተካሄደው ጭፋጨፋ ከ400 በላይ የተማሩ የአኙዋክ ወንዶች ላይ ያተኮረ እንደነበር በተለያዩ ጊዜያት የወጡ ዓለም አቀፋዊ ሪፖርቶችና የጉዳዩ ሰላባዎች ይፋ ያደረጉት ጉዳይ ነው። አቶ መለስ ሞት ቀደማቸው እንጂ የዓለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት የቀረበባቸውን የክስ ማስረጃ ተቀብሎ ክስ እንዲመሰረትባቸው ከድምዳሜ መድረሱም ይፋ ሆኖ ነበር። ኢህአዴግ በዚሁ ፍርድ ቤት ላይ የአፍሪካ መሪዎችን የማስተባባርና የፍርድ ቤቱን አካሄድ ማውገዝ የጀመረው አቶ ኦባንግ የሚመሩት የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ አቶ መለስ ላይ የመሰረተው ክስ እንዲከፈት መወሰኑን ተከትሎ እንደሆነ በወቅቱ ከየአቅጣጫው አስተያየት የተሰጠበት ጉዳይ ነው።
ከዚህ “ዘግናኝ” እንደሆነ ከሚነገርለት ጭፍጨፋ በኋላም በጋምቤላ ሰፋፊ ለም መሬትን በኢንቨስትመንት ስም ነዋሪዎችን በሃይል እያፈናቀለ በመሸጡ ኢህአዴግ ይከሳሳል። በተለይም የኦክላንድ ተቋምና (Oakland Institute) ዓለምአቀፉ የሰብዓዊ መብት ጥበቃ ድርጅት (Human Rights Watch) ያቀረቡዋቸው ሪፖርቶች ኢህአዴግ በስድብና “የአብዮታዊ ዴሞክራሲ መንገድ ተጻራሪዎች፣ ርዕዮተ ዓለሙ ላይ የተነሱ፣ አይኗ እየበራ ያለችውን ኢትዮጵያን ለማጥፋትና ወደኋላ ለመጎተት ልዩ ተልዕኮ ያላቸው፣ የነፍጠኛውን ስርዓት መልሶ ለመትከል የሚሰሩ፣ ጸረ ልማቶች፣ ወዘተ” በማለት ቢያጣጥላቸውም ቀን ጠብቀው ስራቸውን እየሰሩ ስለመሆናቸው እየተነገረ ነው።

Tuesday, February 18, 2014

ኢህአዴግ ራሱ ባወጣው አፋኝ ሕግ ታፈነ


ለተፈጥሮ ሃብት የጠየቀው ዓለምዓቀፋዊ እውቅና ውድቅ ሆነ

eiti
ኢህአዴግ የተፈጥሮ ሃብትን በትክክለኛ መንገድ ለሕዝብ ጥቅም መዋሉን በመከታተል ለአገራት እውቅና የሚሰጠው The Extractive Industries Transparency Initiative (EITI) ለተሰኘ ዓለም ዓቀፋዊ ተቋም ያቀረበው የእውቅና ጥያቄ ማመልከቻ ከተገመገመ በኋላ መመዘኛዎቹን ማሟላት ባለመቻሉ መውደቁ ተሰማ። ኢህአዴግ የእውቅና ማመልከቻ በድጋሚ ማስገባቱን አስቀድሞ ያወቀው ዓለምአቀፉ የሰብዓዊ መብት ጥበቃ ድርጅት (Human Rights Watch) ጉዳዩን ከሚከታተሉ ጋር ባገኘው መረጃ ኢህአዴግ የEITI መስፈርት የማያሟላና በሰብአዊ መብት ጥሰት የተወነጀለ ድርጅት መሆኑንን ማስረጃ አስደግፎ በመጥቀስ መሟገቻ ደብዳቤ ለድርጅቱ አስገብቶ ነበር።
EITI የዛሬ 11ዓመት አካባቢ የተቋቋመ በተፈጥሮ ሃብት ዙሪያ ዕውቅና የሚሰጥ ድርጅት ነው፡፡ ድርጅቱ የተፈጥሮ ሃብት የህዝብ መሆኑን የሚያምን ሲሆን ማንኛውም የተፈጥሮ ሃብት – ማዕድን፣ ዘይት፣ ብረታብረትና ጋዝ – ከመሬት በሚወጣበት ጊዜ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ የሚኖረውን ያህል ግልጽነትና ተጠያቂነት በሌለባቸው አገራት ድርጊቱ ለሙስና እና ግጭት በር እንደሚከፍት ይናገራል፡፡ በመሆኑንም ድርጅቱ አገራት ለሚያቀርቡት የዕውቅና ጥያቄ ማሟላት ያለባቸውን መስፈርት በዝርዝር አስቀምጧል፡፡ ልማትና እድገት በሚል ሰበብ የሕዝብ ሃብት የሆነውን የተፈጥሮ ሃብት በማውጣት የህዝባቸውን መብት ለሚረግጡ አገራት የሚያቀርቡትን የዕውቅና ማመልከቻ ውድቅ ያደርጋል፡፡
የጎልጉል የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ምንጭ እንደጠቆሙት ኢህአዴግ ያቀረበው የእውቅና ጥያቄ ውድቅ መደረጉ እውነት ነው። ምንጩ እንዳሉት ኢህአዴግ በውሳኔው በመበሳጨት ይግባኝ ለመጠየቅ በዝግጅት ላይ ነው። ድርጅቱ (EITI) አንድ አገር ለሚያቀርበው የእውቅና ማመልከቻ በመስፈርቱ መሰረት ግምገማ ካካሄደ በኋላ እውቅና እንዲሰጥ ሲያምን በራሱ ድረገጽ ላይ የዚያን አገር ስም በመመዝገብ ተጠቃሹ አገር ከተፈጥሮ ሃብት ጋር በተያያዙ ኢንቨስትመንቶች የሚገኘው ትርፍ ለህዝብ ጥቅም እንዲውል ያደርጋል የሚል እውቅና በመስጠት ምስክርነቱን ያሰፍራል፡፡

Tuesday, February 11, 2014

ልፋ ያለው በሕልሙ ዳውላ ይሸከማል! ጠርናፊና ተጠርናፊ


ፕ/ር መስፍን ወልደ ማርያም

logopresentation
ሰሞኑን እንደአዲስ ሆኖ የሚወራው ስለጥርነፋ ነው፤ ጥርነፋ ከዲያብሎስ ፋብሪካ የወጣ የክፋትና የጭቆና መሣሪያ ነው፤ ሰዎችን በመጨቆንና በማሰቃየት፣ ምቾትና እንቅልፍ በማሳጣት፣ ፍርሃትንና ስጋትን በማሰራጨት ሕዝብን ለጥ-ጸጥ አድርጎ ለመግዛት የሚፈልጉ ጠርናፊዎች፣ አምባ-ገነኖች፣ ጨቋኞች፣ አፋኞች፣ ዘራፊዎች፣ ወሮበሎች፣ ምድራዊም ሆነ ሰማያዊ ሕግ የማይገዛቸው፣ አምላካቸው አድርገው የሚያገለግሏቸው ሎሌዎችን በሆዳቸው ገዝተው የሚያሰልፉ ናቸው፤  እንኳን የገጠር ልጆችና አኛም የአዲስ አበባዎቹ መሰንከል ምን እንደሆነ እናውቃለን፤ እንስሳትን (በቅሎዎችንና አህዮችን፣ አንዳንዴ በገግና ፍየልም) የፊት እግር ከኋላ እግር ጋር በአጭር ገመድ እያሰሩ እንደልባቸው እንዳይንቀሳቀሱ ማድረግ ነው፤ ሀብት በመሆናቸው ቢጠፉ ባለቤቶቹ ይጎዳሉ፤ ስለዚህ በየአካባቢያቸው ያለውን እየጋጡ ችለው እንዲኖሩ ለማድረግ ቀላሉ ዘዴ መሰንከል ነው፡፡
ለሰውም ቢሆን ዓላማውም ዘዴውም አንድ ነው፤ ልዩነቱ የሰው ልጅ እንቅስቃሴው አካላዊ ብቻ ሳይሆን አእምሮም መንፈስም ስላለው መሰንከሉ አካላዊ ብቻ አይሆንም፤ እንዳያስብ አእምሮውን ማፈን ግዴታ ይሆናል፤ ለአምባ ገነኖች ችግር የሚመጣው የሰዎች አእምሮ ሲያስብ ነው፤ ያሰበውንም መናገርና መጻፍ ሲጀምር ነው፤ ‹‹መጥፎ ሀሳብ››፣ ማለትም ለጨቋኞቹ የማይበጅ ጥሩ ሀሳብ በንግግር፣ በጽሑፍ፣ በራድዮና በቴሌቪዥን ቢተላላፍና ብዙ ሰዎች ቢሰሙት አገር ይረበሻል፤ ሰው ሁሉ ሽብርተኛ ይሆናል፤ አገዛዙ ሕዝቡን ለመሰንከል ብዙ ዘዴዎች አሉት፤ በስም ማጥፋት እንዳልከሰስ ዘዴዎቹን አልናገርም፤ ነገር ግነ ክፉ እንቅልፍ ይዞት የሄደ ካልሆነ በቀር የማያውቃቸው የለም፤ የማያውቅ ካለ በየቤቱ እየመጡ ይተዋወቁታል፡፡

Sunday, February 9, 2014

የአፍሪካ 100 ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች


አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ - 53ኛ!!

aa university
በዓለማችን የሚገኙ የትምህርት ተቋማትን በማወዳደር ደረጃ የሚያወጣው (4 International Colleges & Universities (4icu)) የአፍሪካ ምርጥ የተባሉትን ዩኒቨርሲቲዎችን ዝርዝር ከጥቂት ሳምንታት በፊት አውጥቶ ነበር፡፡ ድርጅቱ በርካታ መረጃዎችን በመሰብሰብ እንዲሁም ለማንም ወገን ያላዳላ ጠለቅ ያለ ሒሳባዊ ትንታኔ በማድረግ ደረጃውን እንደሚያወጣ በድረገጹ ላይ ጠቁሟል፡፡
ከአንድ እስከ ሃያ ባሉት ዝርዝር ውስጥ የደቡብ አፍሪካና የግብጽ ዩኒቨርሲቲዎች ደረጃውን በብዛት ተቀራምተውታል፡፡ ታንዛኒያ፣ ናይጄሪያ፣ ዩጋንዳ፣ ቦትስዋና እና ኬኒያ እስከ ሃያ ባለው ደረጃ በመግባት የአገራቸውን የትምህርት ተቋማት ብቃት አስመስክረዋል፡፡
ከተመሠረተ 60ዓመታት ያለፉት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ (በቀድሞ ስሙ የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዩኒቨርሲቲ) እስከ መቶ ባሉት ዝርዝር ውስጥ የ53ኛ “ክብር” ተጎናጽፎዋል፡፡ ከተመሠረቱ ጥቂት ዓመታት በሆናቸው ዩኒቨርሲቲዎች ተበልጦ ለዚህ የበቃው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በቀደምት ዓመታት የበርካታ አፍሪካውያን ኩራት ነበር፡፡
ህወሃት/ኢህአዴግ ሎሌዎቹን ከየቦታው ሰብስቦ ሥልጣን በያዘ ማግስት መጀመሪያ የወሰደው እርምጃ ኢትዮጵያ በከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ያስተማረቻቸውን 42 ምሁራን በሁለት መስመር ደብዳቤ ማባረር ነበር፡፡ በአቶ መለስ ቀጥተኛ ትዕዛዝ ዶ/ር ዱሪ መሐመድ ያባረሯቸው እነዚህ ምርጥ ምሁራን እንደ ምሁርነታቸው በነጻ በማሰባቸውና ተማሪዎችንም እንደዚያው እንዲያስቡ በማድረጋቸው እንጂ በደብዳቤው ላይ እንደተገለጸው ተፈላጊ ባለመሆናቸው እንዳልነበር የታወቀ ነው፡፡
ኢህአዴግ ሥልጣን ከያዘ በየቦታው የፈለፈላቸው የካድሬ ማምረቻ “ዩኒቨርሲቲዎች” ስሙን ከመያዝ በስተቀር እስከ 100 ባሉት ዝርዝር አንዳቸውም ለመገኘት አለመብቃታቸው የኢትዮጵያን የትምህርት ጥራት ምን ደረጃ ላይ እንደደረሰ የሚያሳይ ነው፡፡

ወያኔ: የነፃው ፕሬስ ፀር!


(ቅዱስ ዮሃንስ)

censorship
ነፃ- ፕሬስ ለነፃነት፤ ለፍትህና ለእኩልነት የሚኖረውን አስተዋፅኦ የሚገነዘቡ ገዢዎች ፕሬሱ ለአንባገነንነት አገዛዛቸው የሚመች ስለማይሆን ይፈሩታል፤ ይጠሉታል፤ ያጠፉታል። ወያኔም እያደረገ ያለው ይህንኑ ነው።
ነፃ ፕሬስ የሀሳብ ነፃነት መብት አልፋና ኦሜጋው ነው ብል ማጋነን አይሆንም። የነፃ ፕሬስ መኖር የሚያረጋግጠው ጋዜጠኞች ያለምንም ጭንቀትና ፍርሃት የሚያስቡትን፡ የሚሰማቸውን፡ የሚሰሙትን እንዲሁም ምርምር አድርገው የደረሱበትን ዜናዎች በነፃ ለመፃፍና ለማሰራጨት ብሎም ሕዝብ እንዲወያይበት ለማድረግ ያላቸው ያልተገደበ መብት ነው። ይህም ጤናማ ሕብረተሰብ ለመፍጠር ብቻ ሳይሆን ለእድገቶቹም ጉልህ ድርሻ አለው።  ነፃ ፕሬስ የኃሳብ ነፃነት ተግባራዊ ለመሆኑ ዋስትናም መፈተኛም ነው። ኃሳብን ያለምንም ጭንቀትና ፍርሃት በነፃ ለመግለፅ መቻልና መለዋወጥ እንደ ምግብና መጠጥ፤ ሁሉ ሰብአዊ ክቡርነትን የተላበሰ ሕይወት ለመጎናፀፍም አስፈላጊም ናቸው። ሃሳብን በነፃ የመግለፅ መብት መኖርና ዋስታናው ዴሞክራሲያዊ በሆነ ሕግ መረጋገጥ ማለት ዘላቂነት ላለው ዴሞክራሲያዊ እድገት ለማገኘትም ዋና መሰረት ነው።
የተሳካ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ለመገንባት የነፃ ፕሬስ አስፈላጊነት ትልቅ ቦታ እንዳለው ከልብ ይታመናል፡፡ ያለነፃ ፕሬስ ዴሞክራሲ አለ ብሎ መናገር ማወናበድ እንጅ እውነት ሊሆንም አይችልም፡፡  የነፃ ፕሬስ መኖር በራሱ የዴሞክራሲያዊ ስርዓት መኖር መገለጫ ነውና፡፡ ዴሞክራሲያዊ መንግስት ሲኖርም ነፃ ፕሬስ ይኖራል፡፡ ወደ እኛ ሃገር ስመለስ ግን ነገሮች ሁሉ የተገላቢጦሽ ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡ ወያኔ መንግስት ሆኖ ላለፉት 23 ዓመታት ሃገሪቱን ሲያስተዳድር ዴሞክራሲያዊ ስርዓትን በወረቀትና በቃል እንጂ ከዚያ በዘለለ በተግባር ሲፈፅም አላሳየንም፡፡ ለመተግበር የሞከራቸውንም እንደ ቀንዳውጣ ቀንድ መልሶ ሸሽጎታል፡፡ ስለዚህ በዴሞክራሲያዊ ስርዓት የማያምን አምባገነን ስርአት ስለሆነ ለነፃው ፕሬስ ፀር በመሆን ተገቢውን ጥበቃና እንክብካቤ በመስጠት ፋንታ አጥፊና ደምጣጭ ሆኖ እየሰራ ይገኛል።

Monday, February 3, 2014

ዳር ሆነው የሚመለከቱት የጎሳ ፖለቲካ ምሱ “ደም”!!


(ርዕሰ አንቀጽ)

image1
“ህወሃት” የሚባለው የትግራይ ነጻ አውጪ ትግራይን መቼና ከማን ነጻ እንደሚያወጣ በውል የተቆረጠ ቀን ባይኖርም ህገ መንግስታዊ ዋስትና ግን አለው በሚል እየተተቸ 23 ዓመታትን አስቆጥሯል። አገር እየመራም ነጻ አውጪ፣ በረሃም እያለ ነጻ አውጪ፣ በአህጉርና በዓለም አቀፍ ደረጃ ሲወከልም ነጻ አውጪ!!
ይህንን የተለመደና ግራ የሚያጋባ እውነት ያነሳነው ወደን አይደለም። ይህ የህወሃት ግልጽ መለያና ከመለያው የሚነሳው ትንታኔ ለማንም የተወሳሰበ ይሆናል ብለንም አንገምትም። ኢህአዴግ የሚባለው የ”ሎሌዎች” ስብስብ ያበጀውና የሚመራው ህወሃት ከሌሎቹ በተለየ በነጻ አውጪ ስም 23 ዓመት አገር ሲገዛ ሌሎቹ “የነጻ አውጪ” ስም አለመያዛቸው ግን ሁሌም ሊመረመር የሚገባው ጉዳይ ይመስለናል።
አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ “ነጻ” መውጣት ያለባቸው ህወሃቶች ሳይሆኑ ሌሎች የአገራችን ህዝቦች፣ የትግራይን ንጹሃንን ጨምሮ ነው። ህወሃት ሲጠነሰስ ጀምሮ የነበሩትን ቀደምት አመራሮች በሂደት እየበላ አራት ኪሎ የደረሰው፤ ህወሃት መጥበብ የጀመረው ገና ከጥንስሱ ጊዜ ጀምሮ ነው። ስለ ህዋሃት የሚወጡ የምስክሮች ሪፖርቶችና መረጃዎች እንደሚያረጋግጡት ህወሃት በደም የታጠበ፣ በደም የተለወሰ፣ የበርካታ ንጹሃን ደም ያጨማለቀው፣ ታሪኩ ሁሉ በደም ዙሪያ የተሰራ፣ አሁንም ከዚሁ የደም ቁማር ነጻ መሆን ያልቻለ መሆኑን ነው።